Thursday, February 11, 2016

አመራሮቻቸውን በገመገሙ ዜጎች ላይ የበቀል እርምጃ እየተወሰደ ነው

የካቲት ፬ (አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በመልካም አስተዳደር ችግሮች ዙሪያ ለውጥ አመጣለሁ በማለት በየአካባቢው ህዝባዊ ስብሰባዎችን እንዲያደርጉ የታዘዙት አመራሮች በርካታ ሚስጥሮች ስለወጣባቸው በጠቋሚዎች ላይ የብቀላ ድርጊት እየፈጸሙ መሆኑ ተነገረ።
በደቡብ ጎንደር እብናት ከተማ በቅርቡ የአስፋልት መንገድ የሚያገኛትና ዘረፈ ብዙ ጥቅሞች እንዳሏት የተገነዘቡት የከተማዋ አመራሮች በከፍተኛ ደረጃ የመሬት ሽያጭ በማካሄድ የሰሩትን የሙስና ስራ ለማጋለጥ የሞከሩትን ባለሙያዎችና ነዋሪዎች ለመበቀል እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ሰሞኑን በተካሄዱ ህዝባዊ ስብሰባዎች መነገሩን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመላከተ።
በደቡብ ጎንደር ዞን ልዩልዩ ከተማዎች በመልካም አስተዳደር ችግሮች ዙሪያ በተደረ...ጉ ስብሰባዎች በባለስልጣናቱ ላይ ጥቆማ የሰጡ ወጣቶችንና ባለሙያዎችን በአደባባይ «በጥይት በሏቸው! »»እስከ ማለት የደረሱ የወረዳ አመራሮች እንዳሉ ቅሬታ አቅራቢዎች ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡
ቅሬታ አቅራቢው አክለውም ጉዳዩ ክልል ድረስ ቢሰማም ጉዳዩን ከወረዳ እስከ ዞን አመራሮች የሚያነካካ በመሆኑ እስካሁን ምንም ዓይነት ርምጃ አለመወሰዱ ያሳዘናቸው መሆኑን ተናግረው ጠቋሚዎቹ በሃሰት ተወንጅለው በክስ ላይ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና በፎገራ ወረዳ የሚገኙ አመራሮች የተሳሳተ መረጃ ለፍርድ ቤት በመስጠት ፍትህን በማዛባት ላይ መሆናቸውን የሚገልጹት ቅሬታ አቅራቢዎች በክልል ደረጃ ያሉ ባለሙያዎችን እየፈተኑ መሆኑን ተናግረው፣የወረዳው አመራሮች ይህን ለመስራታቸው በይፋ ለማረጋገጥ የሚያስችል መረጃ በእጃቸው እንዳለ ተናግረዋል፡፡
በጋይንት ወረዳ የሚገኙ የአስረዳደርና ጸጥታ ኃላፊዎችና ፖሊሶች መሬትን በህገወጥ መንገድ ከያዙ በኋላ ቦታውን እንዲለቁ የሚጠይቁትን ባለሙያዎች በማንገራገር መሬት ያልመለሱበት ሁኔታ እስካሁን ምላሽ ያላገኘ የአደባባይ ሚስጥርነቱ የቀጠለ መሆኑን በቁጭት ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡
«በአዋጅ ቁጥር 11/1ሀ ላይ እና በደንብ ቁጥር 59/99-14/1ሀ ላይ በግልጽ እንደተቀመጠው ማንኛውም ግለሰብ በሌላ ገቢ ላይ የተሰማራ እና በቂ መተዳደሪያ ካለው የገጠር መሬትን ለመተዳደሪያነት በመውሰድ መጠቀም እንደማይችል ቢደነገግም በርካታ ንግድ ፈቃድ አውጠተው የሚሰሩ የከተማ ነጋዴዎች መሬት ይዘው ተጠቃሚ ሲሆኑ ማንነካቸው? » በማለት ቅሬታቸውን በማቅረብ በርካታ ወጣቶች መሬት በማጣት አንድ እድል ያላገኙትን ተጠቃሚ ማድረግ አለመቻሉ ትልቅ ክፍተት መሆኑን ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡

No comments:

Post a Comment