Monday, February 15, 2016

ጋምቤላ በፌደራል ፖሊስና መከላከያ ስር መሆኑዋን መንግስት አመነ

የኮምኒኬሽን ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ በጋምቤላ የአኝዋክና የኑዌር የጸጥታ ሃይሎች ትጥቃቸውን እንዲፈቱ ተደርጎ መከላከያ ካምፕ መግባታቸውን ገልጸዋል። "ይህን ያደረግንበት ምክንያትም ሁለቱ ወገኖች ወደ ለየለት የብሄር መጠፋፋት ሊያመሩ መሆናቸውን ስለደረስንበት ነው" ብለዋል። 
ሚኒስትሩ ሰሞኑን በተደረጉ ውይይቶች ግጭቱን ለማብረድ ችለናል ቢሉም፣ ከአካባቢው የሚደርሱን መረጃዎች ግን አሁንም በየቀኑ ሰዎች እየተገደሉ ነው። ውጥረቱ በየአካባቢው ያለ ሲሆን፣ አንዱ ብሄረሰብ በሚገኝበት አካባቢ ሌላው መጓዝ አይችልም።
ክልሉ ለምን ያክል ጊዜ በወታደራዊ አዛዦች ቁጥጥር ስር እንደሚውል ሚኒስትሩ አልተናገሩም። ጸጥታ ያስከብራሉ ተብለው የሚገመቱት የጸጥታ ሃይሎች የብሄር ግጭት ያስነሳሉ በሚል ትጥቃቸውን እንዲፈቱ ከተደረገ፣ ክልሉ ከእንግዲህ በመከላከያ ስር ሆኖ ይቀጥላል ማለት ነውን፣ ይህን ክልሎች ራሳቸውን ያስተዳድራሉ ከሚለው መብት ጋር እንዴት ነው የሚታየው በማለት ነዋሪዎች በስብሰባዎች ላይ ጥያቄ ማንሳታቸው ታውቋል።
ክልሉ በቅርቡ የብሄር ብሄረሰቦችን ቀን ማክበሩ ይታወቃል። በበአሉ ላይ የተገኙት ባለስልጣናት በክልሉ የሰፈነውን ሰላም እና የተረጋገጠውን መብት በተመለከተ ንግግር አድርገው ነበር። ይሁን እንጅ ሶስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ክልሉ በወታደራዊ ጥበቃ ስር መውደቁ፣ የብሄር ብሄረሰቦችን በአል ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ አገሪቱ ከጸጥታና መረጋጋት ጋር የገባችበትን ችግር እንደሚያሳያስ በክልሉ ውስጥ በአንድ መንግስታዊ ባልሆነ ድርጅት ውስጥ የሚሰሩ ሰው አስተያየታቸውን ለኢሳት አካፍለዋል።

No comments:

Post a Comment