Monday, February 8, 2016

መምህራን አድማ መቱ

ጥር ፴ (ሠላሳ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአማራ ክልል በምስራቅ ጎጃም ዞን ውስጥ የሚገኘው የደብረ ወርቅ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህራን ''የትምህርት ጥራት ይጠበቅ '' በማለት የስራ ማቆም አድማ አድርገዋል።
ዛሬ ጥር 30 ቀን 2008 ዓ.ም ተማሪዎች የአንደኛ ሴሚስተር እረፍታቸውን ጨርሰው ወደ ትምህት ቤቱ ቢያቀኑም መምህራን አድማ በማድረጋቸው በትምህርት ገበታቸው ላይ መገኘት አልቻሉም። ተማሪዎቹ በበኩላቸው ''የትምህርት ጥራት ይጠበቅ!'' የሚለውን መፈክር በማሰማት ወደ ቤታቸው ተመልሰዋል።
አድማውን ከመቱት መምህራን አንዱ ‹‹በክልሉ የሌለ አሰራር በመከተል በትምህርት ቤቱ 4 ምክትል ርዕሰ መምህራን ተሹመውብን ቆይተዋል፤ ይህ መመሪያ ይጥሳል ብለን ታግለን አስወረድናቸው፡፡ ነገር ግን ከወረዱት መካከል አንዱን ርዕሰ መምህር አድርገው እንደገና ሾሙት፡፡ በዚህም ችግሩ ተባብሶ ቀጠለ፤ እኛም ድርጊቱ ትምህርትን ይጎዳል ብለን ከዛሬ ጀምሮ አድማ ልናደርግ ችለናል›› ሲሉ ስለ ሁኔታው ለነገረ-ኢትዮጵያ አስረድተዋል። በትምህርት ቤቱ ውስጥ ካሉ በመቶች ከሚቆጠሩ መምህራን መካከል አብዛሃኞቹ የአድማው ተካፋይ መሆናቸው ታውቋል። የወረዳው ትምህርት ጽሕፈት ቤትና የትምህርት ቤቱ አስተዳደር በበኩላቸው የመምህራኑን ፍትሐዊ ጥያቄዎች ከመመለስ ይልቅ፣ ሰማያዊ ፓርቲን እንጂ ኢህአዴግን አትቀበሉም በማለት ችግሩን ፓለቲካዊ መልክ ለማስያዝ እየሞከሩ መሆኑን ነገረ - ኢትዮጵያ አክሎ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment