Tuesday, February 23, 2016

ከ10 ሚሊዮን በላይ አስቸኳይ የምግብ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች የምግብ አቅርቦት ሊቋረጥባቸው ይችላል ተባለ

ኢሳት (የካቲት 15 ፥ 2008)
በኢትዮጵያ ተከስቶ ባለው የድርቅ አደጋ ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ የተጋለጡ ከ10 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በቀጣዩ ወር የሚቀርብላቸው የምግብ ድጋፍ ሊቋረጥ እንደሚችል የአለም ምግብ ፕሮግራም ማክሰኞ አሳሰበ።
በቀጣዮቹ አስር ቀናት ውስጥ ተጨማሪ አለም አቀፍ እርዳታ ካልተገኘ በርካታ የእርዳታ ማቅረቢያ ጣቢያዎች አገልግሎታቸውን ሊያቋርጡ እንደሚችሉ ዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ የድርጅቱን ሃላፊዎች ዋቢ በማድረግ ዘግቧል።
ሃገሪቱ አለም አቀፍ ማህበረሰብ እየጠበቀች ያለው እርዳታ በአስቸኳይ መቅረብ ካልጀመረ የድርቁ አደጋ አስከፊ ጉዳትን ማድረስ እንደሚጀመር በኢትዮጵያ የአለም ምግብ ፕሮግራም ተወካይ ጆን አይሌፍ ገልጸዋል።

አለም አቀፍ እርዳታ ወደሃገሪቱ ለማድረግ የ120 ቀናትን የሚፈልግ በመሆኑም ህይወትን የመታደግ ስራው መዘግየትን እንዳሳየ ተወካዩ ለጋዜጣው አስረድተዋል።
በተለይ በድርቁ ሳቢያ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰባቸው ያሉ ህጻናት በእርዳታ አቅርቦቱ መዘግየት ግንባር ቀደም ተጎጂ እንደሚሆኑ የአለም ምግብ ፕሮግራም አስታውቋል።
በድርቁ ከፍተኛ ጉዳት በደረሰባቸው የአፋርና የሶማሊ ክልል የሚገኙ አርብቶ አደሮች በበኩላቸው አስቸኳይ የምግብ ድጋፍ መቅረብ ካልጀመረላቸው የእንስሶቻቸው እጣ ፈንታ እንደሚጠብቃቸው ለጋዜጣው ተናግረዋል።
ከነበሯት 200 በግና ፍየሎች መካከል አምስቱ ብቻ እንደቀሩ ያስታወቀችው የአካባቢው ነዋሪ አሻ አብደላሂ የልጆቿን ህይወት ለመታደግ ስትል ቀየዋን ጥላ ወደ ምግብ ማከፋፈያ ጣቢያ መሰደዷን ገልጻለች።
በርካታ አለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች በበኩላቸው ይኸው በስድስት ክልሎች ጉዳትን ኣያደረሰ ያለው የድርቅ አደጋ ወደረሃብ ሊለወጥ ይችላል የሚል ስጋት ማሳደሩን በመግለጽ ላይ ናቸው።
የመንግስት ባለስልጣናት በበኩላቸው ድርቁ ወደረሃብ ሊለወጥ ይችላል የሚለው መረጃ የተጋነነ በማለት በሃገሪቱ ረሃብ አይከሰትም ሲሉ ምላሽን ሰጥተዋል።
ሃገሪቱ ከሚያስፈልጋት ከ1.4 ቢሊዮን ዶላር የምግብ አቅርቦት ውስጥ ከግማሽ በታች የሆነው ብቻ ሊገኝ መቻሉንም ለመረዳት ተችሏል።

No comments:

Post a Comment