Tuesday, February 2, 2016

ኢትዮጵያ በኢንተርኔት ተጠቃሚ ብዛትና ስርጭት ከደቡብ ሱዳን እንደምታንስ አንድ ጥናት ጠቆመ

ጥር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በዓለም ላይ ካሉ አገራት በቴክኖሎጂ ስርጭትና በሃብት ድርሻ ኋላቀር የሚባሉት አገራት የሚገኙበት የምስራቅ አፍሪካ ቀንድ ነው። በቀጠናው በኢንተርኔት ስርጭት ላይ በተደረገ ጥናት ኢትዮጵያ ከአዲሲቷ አገር ደቡብ ሱዳን ባነሰ የኢንተርኔት ስርጭትና ተጠቃሚ ብዛት ያላት አገር መሆኗ ታውቋል።
በመንግስት ባለቤትነት የሚተዳደር አንድ የኢንተርኔትና የስልክ ድርጅት ኢትዮ ቴሌኮም ያላት ኢትዮጵያ ከዘጠና ሚሊዮን በላይ ከሚሆነው ሕዝቧ ውስጥ 3.7 በመቶ ብቻ የኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚ ነው። ጎረቤት አገር ኬንያ 69.6 በመቶ የሚሆነው ሕዝቧ የኢንተርኔት አገልግሎት ተቋዳሽ ከመሆኑም በተጨማሪ የተለያዩ አማራጮች እንዳ...ሉት ተገልጿል። ደቡብ ሱዳን 15.9 በመቶ የኢንተርኔት አገልግሎት ለሕዝቦቿ በማሰራጨት ከኢትዮጵያ በተሻለ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።
ከመቶ ዓመታት በፊት የስልክ አገልግሎት ተጠቃሚ የሆነችው ኢትዮጵያ፣ ከደቡብ ሱዳን ባነሰ የኢንተርኔት ስርጭት ላይ ከመገኘቱዋም በተጨማሪ በማኅበራዊ ድረገጾች የሚጽፉ ጋዜጠኞችን በመሰለል የፕሬስ አፈና እንደምትፈጽም ጥናቱ አመላክቷል። ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በፌስ ቡክ ገጹና በዓምደ መረብ ላይ በመጻፉ ብቻ የ18 ዓመት እስራት እንደተፈረደበት ማዘርቦርድ አስታውቋል።
በኢትዮጵያ ያለው የኢንተርኔት ጠለፋ የከፋ ሲሆን የቀጥታ መስመር ግንኙነቶች ሳንሱር ይደረጋሉ። አገልግሎቱም ዘገምተኛና ጥራት የሌለው እንደሆነ ጥናቱ አክሎ አመላክቷል።
የኢትዮጵያ መንግስት የኢንተርኔት አገልግሎቱን በሞኖፖል መቆጣጠር የፈለገው ጋዜጠኞችን፣የሰብዓዊ መብት ተሟጓቾችንና የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን ለማፈን መሆኑንና የደኅንነት ኃይሎች የግለሰቦችን ቀጥታ ግንኙነት በመጥለፍ ተቃዋሚዎችን በሽብርተኝነት ለመክሰስ እንደሚያውለው ጥናቱ አክሎ አመላክቷል።
የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ልጅ የዘጠኝ ዓመቱ ታዳጊ ናፍቆት እስክንድር እስር ቤት ውስጥ መወለዱ ሳያንስ ፣ አባቱ ከትምህርት ቤት ሲወጣ ሊወስደው ሲመጣ በደኅንነት ኃይሎች በአሰቃቂ ሁኔታ ከአጠገቡ በካቴና ታስሮ በወሰዱ ምክንያት ጋዜጠኝነት ወንጀለኝነት እንደሆነ እንዲያስብ እንዳደረገውም አትቷል።

No comments:

Post a Comment