Tuesday, February 9, 2016

ጸረ ሙስና የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ለመቆጣጠር አልቻልኩም አለ

የካቲት ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የፌዴራል የስነምግባርነሰ የጸረ ሙስና ኮሚሽን በመንግስት መ/ቤቶች ሙስናን ለመዋጋት ያዋቀራቸው የስነምግባር መከታተያ ክፍሎች ውጤት እንዳላመጡ ከኮምሽኑ የተገኘ ሪፖርት ጠቁሟል።
ኮምሽኑ በመንግስት መ/ቤቶች የስነምግባር አውታሮችን በማደራጀትና በመደገፍ ሙስናን የመዋጋት ሚናቸውን እንዲወጡ ክፍሎቹን በሰው ሀይልና በቁሳቁስ እንዲደራጁ ቢያደርግም በተለያዩ ምክንያቶች ዉጤታማ መሆን አልቻሉም። ከእነዚህ ምክንያቶች መካከል የሙስና ወንጀልን ከማጋለጥ ይልቅ ተባባሪ መሆን፣ የሙስና ክሶችን መደበቅ፣ ከማኔጅመንት አባላት ጋር በመሞዳሞድ ሽፋን መስጠት፣ ችግሮችን በምን ቸገረኝነት አይቶ እንዳላየ ማለፍ፣ በሰራተኛው ዘንድ የስነምግባር መኮንኖቹን እንደ...ፖለቲካ ተሹዋሚ በማየት የመገለል ጫና መኖሩና የመሳሰሉት ችግሮች ተነስተዋል።
የአንድ መንግስታዊ መ/ቤት የስነምግባር መኮንን በሰጠው አስተያየት ተጠሪነቱ ለመ/ቤቱ ዋና ስራ አስኪያጅ መሆኑ፣ በአንጻሩ በማኔጅመንቱ የሚሰሩ የስነምግባር ጉድለቶችንና የሙስና ወንጀሎችን እንድንታገል መታሰቡ እርስበርሱ የሚጋጭ በመሆኑ መኮንኑ ስራውን ላለማጣት ሲል መጋጨትን አይፈልግም ብሎአል።
የመንግስታዊ ተቁዋማት የስነምግባር መከታተያ ክፍሎች ውጤታማ አለመሆን ሙስናና ብልሹ አሰራር እንዲሰራፋ አንድ ምክንያት ነውም ተብሎአል። በፌዴራል መ/ቤቶች ብቻ 103 ፣በመንግስት የልማት ድርጅቶች 77፣ በመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች 32፣ በአ/ አ ከተማ አስተዳደር 28፣ በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር 40 በድምሩ 280 የስነምግባር መከታተያ ክፍሎች መኖራቸው ታውቆአል።

No comments:

Post a Comment