Tuesday, July 26, 2016

አቶ ሃብታሙ አያሌው ተጨማሪ ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጠው

ሐምሌ  ፲፱ ( አሥራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በከፍተኛ ሕመም በስቃይ ላይ የሚገኘውና በ አገር ውስጥ ታክሞ መዳን እንደማይችል በሕክምና ቦርድ የተፈረመ ማረጋገጫ የተሰጠው አቶ ሃብታሙ አያሌው የተንዛዛ ተደጋጋሚ የጊዜ ቀጠሮ  እየተሰጠው ሕይወቱ አደጋ ላይ ይገኛል። በዛሬው እለት የሀብታሙ አያሌው የሕክምና ጉዳይ ላይ የአቃቤ ሕግን አስተያየት ለመቀበል የተሰየመው ችሎት አቃቤ ሕግ አስተያየቱን በቃል ሊያቀርብ ፈቃደኛ ቢሆንም ችሎቱ በጽሁፍ እንዲቀርብለት ለሀምሌ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ሰጥቷል።

የምእራብ አርሲ ወጣቶችን ለመያዝ የተሰማራው የአጋዚ ጦር ቤት ለቤት በመግባት አሰሳ እያደረገ ነው

ሐምሌ  ፲፱ ( አሥራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በከኮሳ፣ አሰሳና ዶዶላ አካባቢዎች ሃምሌ 18 እንደገና የተጀመረውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ የመንግስት መስሪያ ቤት የወደመ ሲሆን፣ መንገዶችም ተዘግተው የተሽከርካሪ እንቅስቃሴም ተቋርጦ ውሎአል። የፌደራል ፖሊስ አባላት መኪኖች ወደ ከተሞች መግባት ባለመቻላቸው በእግራቸው ተጉዘው ለመግባት የቻሉ ሲሆን፣ ምሽት ላይ ጥይቶችን በመተኮስ ህዝቡን ሲያሸብሩት አምሽተዋል።

ዛሬ ደግሞ ቤት ለቤት እየገቡ ወጣቶችን በማሰር ላይ ሲሆን፣ በርካታ ወጣቶች ጫካ መግባታቸው ታውቋል። እነዚህም ወጣቶች የኢትዮጵያ ህዝብ ለመብቱ እንዲነሳ ጥሪ አቅርበዋል:: በቦረና ዞን በሚዮ እና ድሬ ወረዳዎች ተቃውሞ ሲካሄድ መዋሉንና ህዝቡ ከእንግዲህ በህወሃት አንገዛም በማለት ተቃውሞ ሲያሰማ መዋሉን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
በምስራቅ ሀረርጌ በጋረሙለታ ጉራዋ ወረዳ ዶጉ ወይም አንቦጢቆ በምትባል ከተማ ትናንት ምሽት ላይ ሕዝባዊ ተቃውሞው ተካሂዷል።

በባህርዳር የሚገኙ የመከላከያ ሰራዊት አባላት በጎንደር በህዝቡ ላይ የተወሰደውን እርምጃ ተቃወሙ

ሐምሌ  ፲፱ ( አሥራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የትግራይ ክልል የደህንነትና የፖሊስ አባላት የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት የኮሚቴ አባላትን ለመያዝ ወደ ጎንደር በተንቀሳቀሱበት ወቅት የኮሚቴው አባል የሆኑት ኮ/ል ደመቀ ዘውዴን “ ህገወጥ በሆነ መንገድ አልያዝም” በማለት ተቃውሞ ማሰማታቸውን ተከትሎ፣ በሰሜን ጎንደር ህዝብና በመከላከያ ሰራዊት አባላት መካከል በተካሄደው የተኩስ ልውውጥ 19 የመከላከያ ሰራዊት አባላት ሲገደሉ 18ት ደግሞ መቁሰላቸው ባለፈው ሃሙስ በባህርዳር በሰፈረው የሰሜን ምእራብ እዝ የመከላከያ ሰራዊት ካምፕ ወይም በተለምዶ አጠራር መኮድ በተደረገው ዝግ ስብሰባ ይፋ ሆኗል። ይህን ተከትሎ በተደረገው የሰራዊት ግምገማ ስብሰባውን የሚመሩት  የሰሜን ምእራብ እዝ አዛዥ ሌ/ጄ ብርሃኑ ጁላ  ፣ “ ይህ ሁሉ ሰራዊት ሲጨፈጨፍ ምን ትሰሩ ነበር?” የሚል ጥያቄ በቁጣ ሲያነሱ፣ የሰራዊቱ አባላት ዝምታን በመመርጥ መልስ ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበሩንም።

Friday, July 22, 2016

አባይ ጸሃዬ ከኤርትራ ጋር ወደጦርነት አንገባም አሉ

ኢሳት (ሃምሌ 15 ፥ 2008)

ከኤርትራ ጋር ጦርነት ውስጥ እንግባ እያሉ የሚገፋፉን ጦርነቱ ውስጥ የማይገቡ፣ ሌላው እንዲሞት የሚፈልጉ ወገኖች ናቸው ሲሉ አቶ አባይ ጸሃዬ ገልጹ።
የህወሃት መስራችና አሁንም የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ አባይ ጸሃዬ የህወሃት ደጋፊ ከሆነው አይጋፎረም ጋር ሰሞኑን ባደረጉት በዚህ ቃለምልልስ ሻዕቢያም ሆነ በርሱ የሚደገፉ ሃይሎች ሲተነኩሱን አጸፋ ምላሽ እንሰጣለን፣ ከዚያ በላይ ግን ልማታችንን የሚያደናቅፍ ጦርነት ውስጥ አንገባም, ህዝብም ልጆቻችንን አንገብርም በማለት ይቃወመናል ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

በአቶ ሃብታሙ አያሌው ሊሰጥ የነበረውን የህክምና ጥያቄ ብይን ለሶስተኛ ጊዜ አራዘመ

ኢሳት (ሃምሌ 15 ፥ 2008)

የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሃገር እንዳይወጣ እገዳ ተጥሎበት ለሚገኘው አቶ ሃብታሙ አያሌው አርብ ሊሰጥ የነበረውን ብይን ለሶስተኛ ጊዜ አራዘመ።
የአቶ ሃብታሙ ቤተሰቦች በህክምና የቦርድ አባላት የጸደቀን እና አቶ ሃብታሙ ከሃገር ውጭ እንዲታከሙ የተላለፈን የባለሙያዎች ውሳኔ ከፍርድ ቤት ቢያቀርቡም ፍ/ቤቱ የቀረበለትን ጥያቄ በአዲስ መልክ ለመመልከት ከቀጣዩ ሳምንት (ሃምሌ 19 ፥ 2008) ዓም ተለዋጭ ቀጠሮን እንደሰጠ ከሃገር ቤት የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

በኢትዮጵያ የሚደረጉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች ከቁጥጥር ውጭ ሊሆኑ ይችላሉ ተባለ

ኢሳት (ሃምሌ 15 ፥ 2008)

በኢትዮጵያ ለበርካታ ሰዎች ሞት ምክንያት የሆኑ እና በተለያዩ ክልሎች በመካሄድ ላይ ያሉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በሂደት ከቁጥጥር ውጭ ሊሆኑ እንደሚችሉ አንድ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም አርብ አሳሰበ።
መቀመጫውን በዚህ በአሜሪካ ያደረገውና በሃገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታዎችን ዙሪያ ሪፖርቱን ያወጣው ፍሪደም ሃውስ፣ መንግስት በብቸኝነት ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቁጥጥርን ተግባራዊ ማድረጉ ተቃውሞዎች እንዲቀሰቀሱና እየተባባሱ እንዲሄድ ምክንያት መሆኑን አስታውቋል።

በአንድ ቀበሌ ብቻ 30 ሰዎች በኮሌራ በሽታ አረፉ

ሐምሌ  ፲፭ ( አሥራ አምስት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በኦሮምያ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞን በደራ ወረዳ ወረ መነዬ ቀበሌ ካለፈው ሁለት ሳምንት ጀምሮ በተነሳው የኮሌራ በሽታ 30 ሰዎች ሲሞቱ 94 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ተይዘው እየታከሙ ነው። የአካባቢው ባለሙያዎች መረጃውን እንዳያወጡ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው መሆኑን የገለጹት የኢሳት ምንጮች፣ በሽታው ወደ አጎራባች አካባቢዎች እየተዛመተ መሆኑንም ተናግረዋል።

በርካታ በሽተኞች ወደ ጸበል መሄዳቸውን ተከትሎ በአካባቢው የሚገኘው ጸበል እንዲዘጋም ተደርጓል። በአዲስ አበባ የሚታየው የኮሌራ በሽታ እየቀነሰ የመጣ ቢመስልም በኦሮምያ ግን በሽታው በአስከፊ ሁኔታ እየተስፋፋ ነው።

ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ሄሊኮፕተሮች ተጭነው ወደ ደብረዘይት እየተወሰዱ ነው

ሐምሌ  ፲፭ ( አሥራ አምስት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ሰኔ 7 ቀን 2008 ዓም በኢትዮጵያ አየር ሃይል የድሬዳዋ ምድብ ውስጥ ሄሊኮፕተርን በመሬት ላይ የማሮጥ ስራ ወይንም ኢንጅን ቴስት ረንአፕ (Engine Test Runup) ሲያደርጉ የነበሩት ሌ/ኮሎኔል ፀጋዘዓብ ካሳ ሌሎች ሁለት የቆሙ ሄሊኮፕተሮችን በመግጨታቸው ሶስቱም ሄሊኮፕተሮች ከጥቅም ውጭ ሆነው የቆዩ ሲሆን፣  ሄሊኮፕተሮቹ በከባድ መኪና ተጭነው  ወደ ደብረዘይት አየር ሃይል ምድብ በመጓጓዝ ላይ ናቸው።

የጤንነቱ ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ የሚገኘው አቶ ሃብታሙ አያሌው ከአቃቤ ሕግ ጋር የቃል ክርክር ለማድረግ ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጠው

ሐምሌ  ፲፭ ( አሥራ አምስት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አቶ ሃብታሙ አያሌው ከአገር ወጥቶ እንዲታከም በሕክምና ቦርድ የተፈረመበት ማረጋገጫ ቢሰጠውም ፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በመዝገብ ቤት በኩል ከአቃቤ ሕግ ጋር የቃል ክርክር ለማድረግ ለማክሰኞ ሀምሌ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ሰጥቷል። አቃቤ ሕግ ቅሬታ ባላቀረበበት ጉዳይ ላይ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ከሕግ አግባብ ውጪ ውሳኔ ማሳለፉን ተከትሎ ባለቤቱ ወ/ሮ ቤተልሔም አዛናውን ጨምሮ ወዳጅ ዘመዶቹን እንዳሳዘናቸውና ተስፋ የመቁረጥ ስሜት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል።

የአማራ ክልል ቴሌቪዥን ስርጭት ተቋረጠ

ኢሳት (ሃምሌ 15 ፥ 2008)

የአማራ ክልል ቴለቪዥን የሳተላይት ስርጭት መቋረጡን የአማራ ክልል መገናኛ ብዙሃን ያረጋገጠ ሲሆን፣ ጉዳዩ ከክፍያ ጋር የተያያዘ መሆኑን አመልክቷል። ሆኖም አንዳንድ ምንጮች የስርጭቱን መቋረጥ ከጎንደር ህዝባዊ እንቅስቃሴ ጋር አያይዘውታል።

“የሕዝብን ጥያቄ በሃይል ማንበርከክ ክቶዉንም ኣይቻልም” – ከጠለምት ተወላጆች ዓለም ኣቀፍ ትብብር የተሰጠ መግለጫ

ሓምሌ 12ቀን 2008 ዓ/ም
 ሰሞኑን ፀረ ሕዝቡ የወያኔ ገዢ ቡድን በወልቃይት፥ ጠገዴና በጠለምት የማንነት ጥያቄ ኣስተባባሪ ኮሚቴ የኣመራር ኣባላትን ጨለማን ተገን በማድረግ በድብቅ ኣፍኖ ወደትግራይ ለመውሰድ ጎንደር ከተማ ኣድፍጦ የቆየው ኣፋኝ ነብሰ ገዳይ ቡድን እነዚህን ብርቅየ የሕዝብ ልጆች የወሰደዉ ኢስብኣዊና አረመኒያዊ ተግባር ኣጥብቀን እንቃወማለን።
መሳሪያ ሳይዝ ህጋዊና ሰላማዊ በሆነ መንገድ በደሉንና ብሶቱን ላቀረበ ሕዝብ የሚሰጥ ምላሽ ኣፈና፥ እስራትና ግድያ ሊሆን አይገባዉም ነበር። ይሁን እንጂ ገና ከጅምሩ ሕዝብን ለስቃይ ሃገርን ለጥፋት ለማብቃት ሽንጡን ገትሮ ከሚታገለው ኣረመኒያዊ የወያኔ ቡድን ይህ እንደሚጠበቅ ላፍታ እንኩዋን ኣንዘነጋዉም።

በኦሮሚያ ሕዝባዊው አመጽ እየተቀጣጠለ ነው – በአምቦ ተቃውሞ ተነሳ

(ዘ-ሐበሻ) ትናንት በምስራቅ ሐረርጌ ሂርን ከተማ ውስጥ ባለችው ዲንቁ አካባቢ ወጣቶች እና ታዳጊዎች ከአዋቂዎች ጋር በመሆን ሕዝቡን ሲያሰማ – በተመሳሳይ ቀን በቦረና ተልታሌ አካባቢም እንዲሁ ሕዝቡ እጁን ወደላይ በማጣመር ሲቃወም የዋለ ሲሆን ይህ ዜና እየተጠናቀረ ባለበት ወቅት በአምቦም ተመሳሳይ ተቃውሞ መነሳቱ ታውቋል::
በኦሮሚያ የተጀመረው ሕዝባዊ ቁጣ በየከተማው በተለያዩ ቀናት ላለፉት 8 ወራት ሲካሄድ ቆይቷል:: በተለይም በሃገር ቤት የሚኖሩ ትግሉን ሊመሩ ይችላሉ የተባሉ ታዋቂ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችን በማሰር እንዲሁም ከ400 በላይ ሰላማዊ ዜጎችን በመግደል በኦሮሚያ የተከሰተውን ሕዝባዊ አመጽ ለማብረድ ስር ዓቱ ቢሞክርም አሁንም የሕዝቡ ቁጣ በየቦታው እየተቀጣጠለ ይገኛል::
ዛሬ በአምቦ ከተማ በርካታ ሰዎች ተቃውሟቸውን በማሰማት ከአጋዚ ሰራዊት ጋር ተፋጠዋል:: ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ በአምቦ በተከሰተው ሕዝባዊ ተቃውሞ ስለተጎዳ ሰውና ንብረት የደረሰን መረጃ የለም::

Monday, July 18, 2016

በሶማሊያ የኢትዮጵያ ወታደሮች 13 ንጹሃን ዜጎችን ገደሉ

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ሰላም አስከባሪነት ጦር አሚሶም ስር ሶማሊያ ውስጥ የተሰማራው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ምንም ዓይነት የጦር መሳሪያ ያልታጠቁ 13 ሰላማዊ የሶማሊያ ዜጎች ላይ የጅምላ ግድያ መፈጸሙ ተዘግቧል።

ከባይደዋ ከተማ በስተምእራብ 30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው አውዲኒያ አቅራቢያ የግፍ ግድያው መፈጸሙን የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸው፣ ከሞቱት13 ዜጎች በተጨማሪ ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ዜጎች ላይ ከፍተኛና ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

በጡረታ የተገለሉ የህወሃት የጦር መኮንኖች በአዲስ አበባ ሚስጢራዊ ስብሰባ እያደረጉ ነው

አንድ ሺ ያክል ቁጥር ያላቸው በጡረታ የተገለሉ የህወሃት አባላት የሆኑ ከፍተኛ የጦር መኮንኖች በአዲስ አበባ ከትናንት ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆይ ሚስጢራዊ ስብሰባ በማድረግ ላይ መሆናቸው ታውቋል። ጥሪው የተላለፈው ለትግራይ ተወላጅ የጦር መኮንኖች ብቻ መሆኑ በሰራዊቱ ውስጥ ያለው አለመተማመን እየሰፋ መምጣቱን ያሳያል በማለት የመረጃው ምንጮች አስተያየታቸውን ገልጸዋል።

Friday, July 15, 2016

በሰሜን ጎንደር ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው

ሐምሌ ፰ ( ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ሰሞኑን በጎንደር ከተማ የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ አመጽ ተከትሎ በሳንጃ፣ በዳባት ፣ በደባርቅ እና በሌሎችም አካባቢዎች ከፍተኛ ውጥረት እንዳለ የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።

በአምባጊዮርጊስ ከተማ ዛሬ ጠዋት ህዝባዊ አመጽ የተቀሰቀሰ ሲሆን፣ ወታደሮች ሃይል ተጠቅመው ለማፈን ሞክረዋል። ይሁን እንጅ ውጥረቱ አሁንም ቀጥሎአል። ከፍተኛ ቁጥር ያለው የመከላከያ ሰራዊትና የፌደራል ፖሊስ በጎንደር ከተማ እና በአካባቢው የተሰማራ ቢሆንም ወጣቶቹ ግን ያነሳነው የመብት ጥያቄ ካልተመለሰ ትግሉን እንቀጥላለን ይላሉ።
በሌላ በኩል በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ነዋሪዎች ህዝቡ ባለበት አካባቢ እንዲነሳ ጥሪ እያቀረቡ ነው። በባህርዳር ከተማ ነዋሪ የሆነች አስተያየት ሰጪ ኢሳትን በሚፈለገው መጠን አልቀሰቀሰም በሚል  አስተያየቱዋን ጀምራ  የባህርዳር ወጣት ዳር ሆኖ እየተጠባበቀ ነው ብላለች ።

በምስራቅ ኢትዮጵያ ያለው የርሃብ አደጋ አሁንም አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንዳለ ኦክስፋም አስታወቀ



ሐምሌ ፰ ( ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በኢትዮጵያ ከ10 ሚሊዮን በላይ ዜጎች አፋጣኝ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ኦክስፋምን ገልጾ፣ ባለፈው ዓመት ዝናብ አለመጣሉን ተከትሎ ሰብልቻቸው የወደሙባቸው አርሶአደሮችና የቤት እንስሶቻቸው ያለቁባቸው አርብቶ አደሮች ምጽዋት ጠባቂ ሆነዋል ብሎአል።

ከድሬደዋ 75 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ፊዲቶ የመጠለያ ጣቢያ ውስጥ የሚገኙት 10ሽህ በላይ ተረጅዎች ሲኖሩ የርሃቡ ተጠቂዎች ውስጥ ሕጻናት መኖራቸውንና በተመጣጠነ የምግብ እጥረት ሳቢያ ክፉኛ እንደተጎዱም ሪፖርቱ አመላክቷል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዓለም አቀፉ ማህበረሰብና ግብረሰናይ ድርጅቶች የኢትዮጵያ ድርቅ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መሆኑን ቢናገሩም ገዥው መንግስት ግን ሁኔታዎችን ማስተባበል መምረጡን ችግሩን ማባባሱን ቲአርቲ ሲቲዝን ዘግቧል። ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አይኦኤም በበኩሉ በኢትዮጵያ የተከሰተውን ድርቅ ተከትሎ ከ630 ሽህ በላይ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ብቻ ከመኖሪያ ቀያቸው መፈናቀላቸውን አስታውቋል።

በደቡብ ሱዳን ድጋሚ ባገረሸው የእርስበርስ ጦርነት ኢትዮጵያዊያን አጣብቂኝ ውስጥ ገብተዋል

ሐምሌ ፰ ( ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በደቡብ ሱዳን ያገረሸውን ግጭት ተከትሎ የውጭ አገር ዜጎች በየአገሮቻቸው ኢምባሲ አማካኝነት አገሪቱን ለቀው በመውጣት ላይ ቢሆንም ኢትዮጵያውያን  ግን ተመሳሳይ እርዳታ ባለማግኘታቸው ደህንነታቸው አደጋ ውስጥ ወድቋል።  የአውሮፓ ሕብረት አገራት ዜጎችን ጨምሮ የአፍሪካ አገራት በተለይም ጎረቤት ኡጋንዳና ኬንያ ወታደሮቻቸውን ወደ ደቡብ ሱዳን በመላክ ዜጎቻቸውን ከጥቃት በመከላከል ወደ አገራቸው እየመለሱ ነው።

Thursday, July 14, 2016

በጎንደር የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደ ሌሎች አካባቢዎች እየተዛመተ ነው

ኢሳት (ሃምሌ 7 ፥ 2008)

ከቀናት በፊት በጎንደር ከተማ የተቀሰቀሰዉ ህዝባዊ ተቃዉሞ ሐሙስ ወደ ደባርቅ ከተማና ዙሪያዋ ባሉ አካባቢዎች በመዛመት ላይ መሆኑን ነዋሪዎች ለኢሳት ገለጡ ።
ሰሞኑን በመንግስት የፀጥታ ሀይሎች የተገደሉ ሰዎችን ሐሙስ የቀብር ስነ-ስርአት ቢካሄድም ስነ-ስርአቱ ወደ ተቃዉሞ መቀየሩንና ነዋሪዎች ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ህወሐት)ን የሚያወግዙ  መፈክሮችን ሲያሰሙ መዋላቸዉ ታዉቋል።
በከተማዋ የተሰማራ የፀጥታ ሀይሎች ተቃዉሞዉን ለመበተን አስለቃሽ ጢስን መጠቀም ቢጀምሩም ተቃውሞዉ በቁጥጥር ስር ሊውል አለመቻሉን ለደህንነታቸዉ ሲሉ ስማቸዉን መግለፅ ያለፈለጉ ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልስ አስረድተዋል።

የጎንደር ህዝብ ህዝባዊ ትግሉን እንደሚቀጥል አስታወቀ

ሐምሌ ፯ ( ሰባት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ አቅራቢዎች የኮሚቴ አባላት መታሰራቸውን ተከትሎ በጎንደር ከተማ የተነሳው ህዝባዊ አመጽ፣ በደባርቅ የተደገመ ሲሆን፣ የዳባት ወረዳ ወጣቶችም ወደ ደባርቅ በመሄድ ህዝባዊ አመጽ ጀምረዋል። የወልቃይት ጠገዴን ህዝባዊ ጥያቄ ሲመሩ በመጨረሻም መሳሪያቸውን አንግበው  ሲፋለሙ የተገደሉት  ባለሃብቱ አቶ ሲሳይ ታከለ በጎንደር ከተማ ደማቅ የሆነ የጀግና የቀብር ስነስርዓት ከተደረገላቸው በሁዋላ ፣ የአመጹ አስተባባሪዎች ፣ በእስር ላይ የሚገኙት የኮሚቴ አባላት ካልተፈቱ እንዲሁም የማንነት ጥያቄያቸው ካልተመለሰ አፈሙዛቸውን ወደ ክልሉ መንግስት እንደሚያዞሩ አስጠንቅቀዋል። በአደራ መልክ የተሰጡት ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ለትግራይ ደህንነቶች ተላልፈው የሚሰጡ ከሆነም፣ ትግሉ የመረረ ይሆናል ሲሉ ማስጠንቀቂያ ልከዋል።

በርካታ ቁጥር ያላቸው የፌደራል ፖሊስ አባላት ወደ ጎንደር እያመሩ ነው

ሐምሌ ፯ ( ሰባት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የህወሃት/ኢህአዴግ መንግስት ከወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ህዝባዊ አመጽ ለመቆጣጠር በኦሮምያ፣ በደቡብና መሃል አዲስ አበባ ያሰፈራቸውን የአጋዚ ጦር አባላትንና ወታደሮችን ወደ ሰሜን በማጓጓዝ ላይ ይገኛል።

ሰላማዊ ትግሉን በሃይል ለመጨፍለቅ የወሰነ የሚመስለው ስርዓቱ፣ በተመሳሳይ መልኩ ከታጠቁት የክልሉ ታጣቂዎች ተቃውሞ ይገጥመዋል ተብሎ ይጠበቃል። የክልሉ ነዋሪዎች በጎንደር የተወሰደውን እርምጃ እያወገዙ ሲሆን፣ በአንዳንድ ከተሞች ተቃውሞ ይነሳል በሚል ጥበቃው ተጠናክሯል።

አሜሪካና እንግሊዝ ዜጎቻቸው ወደ ጎንደር እንዳይሄዱ አሳሰቡ

ሐም ፯ ( ሰባት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ተቀማጨነቱ በአዲስ አበባ ከተማ የሆነው የአሜሪካን ኤንባሲ አሜሪካዊያን ዜጎች ወደ ጎንደር ከተማና አካባቢው እንዳይጓዙ ጊዜያዊ የጉዞ እገዳ ጣለ። በተጨማሪም ኤንባሲው በጎንደር አካባቢ ያለው ሕዝባዊ አመጽ እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ ማንኛውም የአገሪቱ ዜጋ ወደ ቀጠናዎቹ እንዳይዘዋወርና በአሁኑ ወቅትም በስፍራው ያሉ ዜጎች እራሳቸውን እንዲጠብቁም ሲል ጥሪውን አቅርቧል።

አርበኞች ግንቦት 7 ለጎንደር ህዝብ አጋርነቱን እየገለጸ እንደሚገኝ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተናገሩ

ኢሳት (ሃምሌ 6 ፥ 2008)

አርበኞች ግንቦት 7 መስዋዕትነት እየከፈለ ለሚገኘው የጎንደር ህዝብ አጋርነቱን እየገለጸ እንደሚገኝ ሊቀመንበሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተናገሩ። የአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በምስልና ድምፅ ከኤርትራ ረቡዕ ዕለት ባስተላለፉት መልዕክት የአማራም ህዝብ ሆነ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ አጋርነቱን እንዲያሳይ ጥሪ አቅርበዋል።

Tuesday, July 12, 2016

የወልቃይት ጥያቄ የሚመሩ የኮሚቴ አባላትን ለመያዝ በተወሰደው ዕርምጃ የሰላማዊ ሰው ህይወት ጠፋ

ኢሳት (ሃምሌ 5 ፥ 2008)
የወልቃይት የማንነት ጥያቄን የሚመሩ የኮሜቴ አባላትን ለማሰር በተወስደ እርምጃ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከፍተኛ ግጭት አስከተለ። ሰላማዊ ሰዎችም የተገደሉ ሲሆን፣ ከህዝብ ወገን በተወሰደ አጸፋ የጸጥታ ሃይሎች መገደላቸውም ታውቋል። የኮሚቴ አባል የሆኑት ኮሎኔል ደመቀ
ዘውዴ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ተከበዋል።

በሰሜን ጎንደር መንግስት ከታጣቂ ሃይሎች ጋር እየተታኮሰ እንደሆነ ገለጸ

ኢሳት (ሃምሌ 5 ፥ 2008)

መቀመጫቸውን በኤርትራ ካደረጉ ሃይሎች ጋር ግንኙነት ኣላቸው የተባሉ ታጣቂዎች በሰሜን ጎንደርና ትግራይ ክልሎች ከመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ጋር የተኩስ ልውውጥ በማድረግ ላይ መሆናቸውን መንግስት ማክሰኞ ምሽት ገልጸ።
ታጣቂዎች ሴቶችንና ህጻናትን ከለላ በማድረግ ከመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ጋር ተኩስ በመክፈትና ቦንብ በመወርወር ጉዳት አድርሰዋል ሲል የብሄራዊ መረጃ ደህንነት አገልግሎትና የፌዴራል ፖሊስ የጋራ የጸረ-ሽብር ግብረሃይል አስታውቋል።

ጎንደር በተኩስ እየተናጠች ነው

ኢሳት (ሃምሌ 5 ፥ 2008)

በጎንደር ከተማ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ቁጣ የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ኤፈርት ንብረት የሆነው ሰላም ባስን ጨምሮ የንግድ ተቋማት መቃጠላቸው ተሰምቷል። ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ እጅ አልሰጥም በማለት መታኮሳቸው የታወቀ ሲሆን፣ ከጎንደር ከተማና አካባቢም በርካታ ነዋሪዎች ዕርሳቸውን ለመታደግ ተንቀሳቅሰዋል።
በከተማዋ ሙሉ በሙሉ የንግድ እንቅስቃሴ ሆነ ስራ የቆመ ሲሆን፣ ኮ/ል ደመቀ ዘውዴን ለመታደግ የወልቃይት ጠገዴ ተወላጆች በ6 አውቶቡሶች ወደጎንደር መንቀሳቀስ የጀመሩ ሲሆን፣ ከተለያዩ የአማራ አካባቢዎች ህዝብ ድጋፉን ለመግለጽ ወደ ጎንደር በመንቀሳቀስ ላይ መሆኑ ተሰምቷል። ራቅ ባሉ አንዳንድ የአማራ አካባቢዎችም በየአካባቢው እንቅስቃሴ መታየት መጀመሩን ለኢሳት የደርሰው ዜና ያስረዳል።

Monday, July 11, 2016

በፈተና ስም ማህበራዊ ሚዲያው አፈና ተካሄደበት

ሐም ( አራት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በመላ አገሪቱ የፌስ ቡክ፣ ትዊተር፣ ኢንስታግራም እና ቫይበር የመልክት መለዋወጫ ዘዴዎች የተዘጉ ሲሆን፣ ገዢው ፓርቲ እርምጃውን የወሰድኩት የአስራ ሁለተኛ ክፍል ተማሪዎች ተረጋግተው ፈተና እንዲፈተኑ ለማስቻል ነው ብሎአል።

ይሁን እንጅ እርምጃው በአገሪቱ ውስጥ እየተባባሰ ከመጣው የፖለቲካ ቀውስ ጋር እየተያያዘ ነው። ገዢው ፓርቲ ለፈተና በሚል አለማቀፍ ገጽታውን አያበላሽም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች፣ ምክንያቱ የማህበራዊ ሚዲያው እየፈጠረ ካለው ተጽኖና በአገሪቱ እየታዬ ካለው አለመረጋጋት ጋር የሚያያዝ ነው በማለት አስተያየት ይሰጣሉ።

በአርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ 44 የመድረክ አባላት አርሶአደሮች ታሰሩ

ሐም ( አራት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ አርሶአደሮቹ የታሰሩት ማዳበሪያ አንወስድም ብለዋል የሚል ክስ ተመስርቶባቸው ነው ። ከታሰሩ 10ኛ ቀናቸውን የያዙት አርሶአደሮች ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል። ከታሰሩትም መካከል የ80 ዓመት አዛውንትም ይገኙበታል። የአካባቢው የመድረክ ተወካይ እንደገለጹት አርሶአደሮቹ ማዳበሪያውን ለመውሰድ ያልፈለጉበት ምክንያት “ ተመጣጣኝ ዝናብ የለም፣ አንድ ጊዜ ከከፈልን በኋላ በተደጋጋሚ ክፍያ እንጠየቃለን “ የሚል ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም በማዳበሪያ እዳ ሲሰቃዩ መቆየታቸውን ገልጸዋል። አድኑን ብለው መድረክ ጽ/ቤት መሄዳቸውን የገለጹት ተወካዩ፣ ፖሊሶቹ ጽ/ቤቱ ድረስ ገብተው አርሶአደሮችን አፍነው ወስደዋቸዋል ብለዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ የወረዳውን ፖሊስ አዛዥ ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።

አቶ አንዳርጋቸው የማይቀርቡ ከሆነ እስረኞችን በነጻ እፈታለሁ ሲል ፍርድ ቤቱ ማስጠንቀቂያ ላከ

ሐም ( አራት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በዘመነ ካሴ መዝገብ በሽብር ወንጀል ተከሰው ከአመት በላይ በእስር ቤት በስቃይ ላይ የሚገኙት አቶ አሸናፊ አካሉ ፣ ደህናሁን ቤዛ፣ ምንዳየ ጥላሁንና አንሙት የኔዋስ፣ በመከላከያ ምስክርነት የጠሩዋቸው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንደቀርቡላቸው በተደጋጋሚ ቢጠይቅም፣ ቃሊቲ እስር ቤት ለማቅረብ ፈቃደኛ አለመሆኑን ተከትሎ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ለእስር ቤቱ ሃላፊዎች “ ለምን ሰው ይንገላታል፣ ሰበር ሰሚ ችሎት ሳይቀር እንዲቀርብ የወሰነው ለምን አይቀርብም፣ እናንተ አላቀርብም በማለታችሁ ተከሳሾች አንድ አመት በእናንተ የተነሳ እየተንገላቱ ነው” በማለት ከተናገረ በሁዋላ፣ አቶ አንዳርጋቸው ሃምሌ 7 ቀን 2008 ዓም ፍርድ ቤት የማይቀርቡ ከሆነ ተከሳሾችን በነጻ እናሰናብታለን ሲል ሰኔ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።

ዜጎችን ማፈናቀል መግደልና ማሰደድ የህወሃት አይነተኛ መግለጫዎች ናቸው!!! (አርበኞች ግንቦት 7)

ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ወደ ስልጣን ከመጣበት ጊዜ አንስቶ በአገራችንና በህዝባችን ላይ ሲፈጽም የቆየውና እየፈጸመ ያለው ግፍና ስቃይ ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደልም። አፈና ፣ እስር፣ ግድያና ዜጎችን ማፈናቀል አይነተኛ መግለጫዎቹ የሆነው ይህ የህወሃት አገዛዝ፣ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችንና የከተማ ቦታዎችን በመቸብቸብ ሃብት ለማካበት ባለው ዕቅድ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን እትብታቸው ከተቀበረበት ቀዬና የትውልድ መንደሮቻቸው በግፍ እንዲፈናቀሉ አድርጎአል። አሁንም እያደረገ ነው ።
ሰሞኑን በአዲስ አበባ በንፋስ ስልክ ክፍለ ከተማ ቀርሳና ኮንቶማ በተባሉ ቀበሌዎች ከ30 ሺ በላይ የሚገመት ህዝብ ለአመታት ከኖረበት መኖሪያ ቤቶች በሃይል ተገፍትረው በመውጣት ጎዳና ላይ እንዲበተኑ ተደርጎአል። በዚህም እርምጃ ምክንያት አቅመደካማ የሆኑ አዛውንቶች፤ ነፍሰጡሮችና ከወለዱ ገና ሳምንታት ያልሞላቸው እመጫቶች፤ የሚያጠቡ እናቶች፤ ህጻናትና ለጋ ወጣቶች ለከፋ ችግር ተዳርገው ለቅሶና ዋይታ በማሰማት ላይ ናቸው ። በስንት ልፋትና ድካም ከሰሩዋቸው ቤቶች ተለዋጭ ቦታ ሳይሰጠን ወይም ካሳ ሳይከፈለን አንወጣም በማለት ለማንገራገር የሞከሩ 10 ሰዎች በፖሊስ ጥይት ተገደለዋል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ደግሞ ለእስር ተዳርገዋል።

Friday, July 8, 2016

ትምህርት ሚኒስቴር የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂ ፈተና መውጣቱን በተመለከተ መግለጫ ለመስጠት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ተማሪዎች ተረጋግተው ለመፈተን አልቻሉም



ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በመጪው ሳምንት መጀመሪያ ላይ የሚሰጠው የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ከፈተናው ቀን በፊት ለኢሳት መላኩን የተመለከተ ዘገባ ከቀረበ በሁዋላ፣ ኢሳት የትምህርት ሚኒስቴር ባለስልጣናት አስተያየት እንዲሰጡበት ለማድረግ ላለፉት 2 ቀናት ተደጋጋሚ ጥረት ሲያደርግ ቢቆይም፣ በሚኒስቴሩ በኩል መረጃ የሚሰጠው አካል ለማግኘት ባለመቻሉ ትክክለኛነቱ ላይ አስተያየት ለመስጠት ሳይችል ቀርቷል።

“ፈተናው ተሰርቆ ወጥቷልና እባካችሁ አጣሩልን” በማለት የጠየቁን ወገኖች፣  26 ገጽ ያለው የእንግሊዝኛ የፈተና ወረቀት በማመሳከሪያነት ከላኩልን በሁዋላ፣ የኢሳት የኢዲቶሪያል ቦርድ መረጃው በኢንተርኔት እንዳይለቀቅ ወስኖ ነበር። ትምህርት ሚኒስቴር የዜናውን ይፋ መሆን ተከትሎ መልስ ባይሰጠም፣ ለኢሳት የደረሰው የፈተና ቅጅ ወረቀት ከትናንት ጀምሮ በኢንተርኔት በስፋት መሰራጨቱን የኢዲቶሪያል ቦርዱ አረጋግጧል።

የአሜሪካ የህግ መወሰኛ ኮሚቴ የውጭ ግንኙነት ክፍል ለኢትዮጵያ የሚሰጠው እርዳታ እንደገና እንዲታይ ጠየቀ

ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የአሜሪካ የህግ መወሰኛ ምክር ቤት አባላት ( ሴናተሮች) የህወሃት/ኢህአዴግ መንግስት የሚፈጽመውን የሰብአዊ መብት ጥሰት አውግዘዋል።

የሴኔቱ የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ የኦባማ አስተዳደር ለኢትዮጵያ የሚሰጠው እርዳታ እንደገና እንዲመረመር የቀረበለትን ፕሮፓዛል ደግፎ ሙሉ ቤቱ እንዲወስንበት ውሳኔውን አስተላልፏል።

መምህር አብረሃ ደስታ ከእስር ተፈታ

ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከሃምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ  በሽብር ወንጀል ክስ ተመስርቶበት ላለፉት ሁለት ዓመታት በእስር ሲንገላታ የነበረው የአረና ትግራይ ፓርቲ አባል መምህር አብረሃ ደስታ ከእስር ተፈቷል።

አቶ አብርሃ ደስታ ነሀሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በከፍተኛው ፍርድ ቤት ከተከሰሰበት የሽብር ወንጀል ነጻ የተባለ ቢሆንም፣  ችሎት ተዳፍረሃል ተብሎ ለተጨማሪ ጊዜያት በእስር እንዲቆይ ተደርጓል። አብርሃ ደስታ የህወሃት ኢህአዴግ መንግስት በተለይ በትግራይ ክልል ውስጥ የሚፈጽማቸውን ኢሰብዓዊ ድርጊቶች ሲያጋልጥ ቆይቷል።

የመምህራን ሽልማት ቅሬታ አስነሳ

ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ባህርዳር ሙሉዓለም አዳራሽ  ሃምሌ 30/ 08 ዓ.ም በተደረገው የምስጉን መምህራን ሽልማትአሰጣጥ ላይ የተገኙ መምህራን፣ ሽልማቱ የተሰጠው በብአዴን ፓርቲ ውስጥ አባል በመሆን አስተዋጽዎ ላበረከቱት እንጅ በሙያቸው ላገለገሉት አይደለም በማለት ቅሬታቸውን ገልጸዋል።

መምህራኑ እንደተናገሩት ሽልማት የተሰጣቸው በስራቸው ታታሪ ለሆኑ መምህራን ሳይሆን  በገዥው ፓርቲ ውስጥ አባል በመሆን ለተንቀሳቀሱ መምህራን ብቻ ነው። በተካሄደው የሽልማት አሰጣጥ ፕሮግራም ሁሉም የባህርዳር አስተዳደር መምህራን እንዲገኙ ጥሪ ቢተላለፍም፣  ከድርጅቱ አባላት ውጭ የተገኙ በጣት የሚቆጠሩ መሆናቸውን የተናገሩት ቅሬታ የተሰማቸው መምህራን፤ የክልሉ መንግስት የመምህራንን የሙያ ማህበር በራሱ አባላት በመሙላት የተለያዩ ጥቅማ ጥቅም በሚሰጥበት ጊዜ ለፓርቲው ታማኝ የሆኑትን ብቻ በመምረጥ የታታሪ መምህራንን ሞራል ሲነካ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

የአፍሪካ ኅብረት የሰላም አስከባሪ ጦር አሚሶም በሶማሊያ ቆይታውን አራዘመ ውሳኔውን ሂውማን ራይትስ ወች አወገዘ

ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በሶማሊያ ዘላቂ ሰላም ያመጣል ተብሎ ወደ ሶማሊያ ያመራው የአፍሪካ ኅብረት የሰላም አስከባሪ ጦር አሚሶም  በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ በአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ማስፈን እንዳልቻለ ተገልጿል። የኅብረቱ ጦር ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ 22 ሽህ ሰራዊቶች ቢኖሩትም እስከ 2018 እ.ኤ.አ. በአገሪቱ ተልእኮውን አጠናቆ ለሶማሊያ ጦር አስረክቦ ይወጣል ሲባል የቆየ ቢሆንም ከአልሸባብ ተዋጊዎች በገጠሙት የተለያዩ ተግዳሮቶች የመቆያ ጊዜውን እስከ 2020 እ.ኤ.አ.  ድረስ ለማራዘም ተገዷል።

በተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት ፍቃድ 2007 እ.ኤ.አ. የተቋቋመውን አሚሶንን በዋናነት ሲረዳ የነበረው የአውሮፓ ኅብረት እገዛውን 20 % ለመቀነስ ውሳኔውን አሳልፏል። አልሸባብ ተገፍቶ የወጣባቸውን የገጠር አካባቢዎች ድጋሜ በእጁ በማስገባት ላይ ሲሆን ኡጋንዳና ኬኒያ በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ጥቃቶችን ተከትሎ በቀጣይ ዓመታት ሶማሊያን ለቀው እንደሚወጡ አስቀድመው አሳውቀዋል። በሶማሊያ ከተሰማሩት የሰላም አስከባሪ ጦር ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ ያላትና ስድስት ሽህ ሰራዊት ያሰማራችው ኡጋንዳ በ2017 እ.ኤ.አ. ሙሉ ለሙሉ ሶማሊያን ለቀው እንደሚወጡ የጊዜ ገደብ አስቀምጠዋል።

Thursday, July 7, 2016

አቶ ሃብታሙ አያሌው ተጨማሪ የሃኪም ማረጋገጫ እንዲያቀርብ ታዘዘ

የፈዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የቀድሞ የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ አመራር አባል አቶ ሃብታሙ አያሌው ወደ ውጭ አገር ሄዶ እንዲታከም ተጨማሪ የሃኪሞች ቦርድ ማረጋገጫ እንዲያቀርብ ጠየቀ።

ሁለት ቤተክርስቲያኖችን ለማፍረስ የተደረገው ሙከራ የህዝብ ቁጣ ቀስቅሷል

ባለፈው ሳምንት በአዲስ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ቀጣና 01 መንደር 06 በተለምዶ አጠራር ቀርሳና ኮንቶማ በሚባለው አካባቢ የሚገኙ ሁለት ቤተክርስቲያኖችን ለማፍረስ የሚደረገውን እንቅስቃሴ ህዝቡ እየተቃወመ ነው።

ባለፈው ሳምንት ኡራኤል ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ ሙከራ ሲደረግ ህዝቡ ባስነሳው ተቃውሞ ቤተክርስቲያኑ እስካሁን ሳይፈርስ ቆይቷል። ከሶስት ቀናት በሁዋላ ደግሞ የቤተክርስቲያኑ ቄስ በፌደራል ፖሊስ ተገድለዋል። አፍራሽ ግብረሃይሎች የጸበል ቦታውን ካፈረሱ በሁዋላ ፣ ሙሉውን ቤተከርስቲያን ለማፍረስ ህዝቡ ጽላት እንዲያወጣ ጠይቀዋል። ይሁን እንጅ ጽላቱን የሚያወጡ ቄሶችን ገድላችሁዋቸዋል በማለት ህዝቡ መልስ የሰጠ ሲሆን፣

የተመድ የምግብና የእርሻ ክፍል በጎርፍ ለተጎዱት ዜጎች ተጨማሪ ገንዘብ ጠየቀ

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብ እና የእርሻ ክፍል በቅርቡ በተከሰተው ረሃብ የተጎዱ ዜጎች ሳያገግሙ በድጋሜ በጎርፍ በመጠቃታቸው ለመስከረም ወር ተጨማሪ የ3 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ጠይቋል።

ድርጅቱ የኢትዮጵያን የጎርፍ አደጋ መከላከል ግብረሃይልን ጠቅሶ እንደዘገበው በጎርፉ ምክንያት 690 ሺ ተፈናቅለዋል።
55 ሺ ሄክታር መሬትም በጎርፍ መጥለቅለቁን ድርጅቱ አስታውቋል።
በድርቁ የተጎዱ ዜጎች ወደ ነበሩበት ቦታ ለመመለስ በትንሹ ሁለት አመት ያስፈልጋቸዋል።
ድርጅቱ የውሃ አቅርቦትን ለመጨመር ተጨማሪ 2 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፍልገውም ገልጿል።

Tuesday, July 5, 2016

የኢህአዴግ መንግስት አብዛኛውን ወታደራዊ ግዥ የሚፈጸመው ከቻይና ኩባንያዎች ጋር መሆኑን ሰነዶች አመለከቱ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ለኢሳት የደረሱት ወታደራዊ የመሳሪያ ግዢን የሚያመላክቱ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ፣ መከላከያ ሰራዊት አብዛኛውን ግዢ የሚፈጽመውም ሆነ የእድሳት ስምምነትና እና የግንባታ ስራ የሚሰራው ከቻይናው North Industies Corporation ወይም በአጭሩ NORINCO ኩባንያ ጋር ነው።

መከላከያ ከዚህ ኩባንያ ጋር በፈረንጆች አቆጣጠር እስከ 2013 ድረስ 440 ሚሊዮን 158 ሺ 409 አሜሪካ ዶላር የሚያወጣ የግዢ ኮንትራት የፈጸመ ሲሆን፣ በአማካኝ እስከ ግማሽ የሚሆነው እዳ ተከፍሏል።

የኦሞ ኩራዝ ስኳር ፋብሪካ ሰራተኞች በወታደሮች ሲዋከቡ ዋሉ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የፋብሪካው ሰራተኞች ለጂንካ ልማት በሚል ያለፈቃዳቸው ከደሞዛቸው እየተቆረጠ መከፈሉን ሲቃወሙ የሰነበቱ ሲሆን ዛሬ ከ200 በላይ ወታደሮች ወደ ፋብሪካው በመግባት ሰራተኞችን ሲያስጨንቁ ውለዋል።

ከደርጃ 1-13 የሚገኙ ሰራተኞች  በአንድ ድምጽ “አንከፍልም” በማለት ስብሰባ ረግጠው መውጣታቸውን ተከትሎ በብሄር እየለዩ ለማጋጨት ሙከራ ሲደረግ መሰንበቱን ሰራተኞች ገልጸዋል። የአማራ ተወላጆች  “ልማት አደናቃፊ እና የድሮ ሥርዓት ናፋቂ “ እየተባሉ ሲዋከቡ የቆዩ ሲሆን የኦሮሞ ተወላጅ ሰራተኞችም እንዲሁ በተቃዋሚነት ተፈርጀው ተዋክበዋል። ማኔጅመንቱ ሰራተኛውን ሳያስፈቅድ ለጅንካ ከተማ ልማት  1.5 ሚሊየን ብር እንከፍላለን ብሎ ቃል መግባቱ የችግሩ መነሻ መሆኑን ሰራተኞች ይናገራሉ።

በአዲስ አበባ ቤታቸው የፈረሰባቸው ነዋሪዎች ቤት መከራየት አለመቻላቸውን ተናገሩ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በክረምት መጠለያ አልባ የሆኑት የቀድሞ የሃና ማርያም አካባቢ ነዋሪዎች፣ ቤት ለመከራዬት እንኳን ስንጠይቅ፣ አከራዮቹ “ ‘እንዳታከራዩዋቸው’ የሚል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶናል”  በሚል ቤታቸውን ሊያከራዩን ፈቃደኞች አልሆኑም ሲሉ ብሶታቸውን ገልጸዋል።

ገዢው መንግስት ወጣቶችን እያደነ ማሰሩን መቀጠሉን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ በእስር እና በግድያ መበቀሉ አንሶ አሁን ደግሞ ቤት እንዳንከራይ በመከልከል የበቀል ጅራፉን እያሳረፈብን ነው ይላሉ። ከቀርሳ ኮንቶማ የመጡትን ወጣቶች እየፈለጉ በማሰር ላይ መሆናቸውን ነዋሪዎች ይገልጻሉ። የፌደራል ፖሊስ አካባቢውን አሁንም ድረስ በመቆጣጠሩ መግባት መውጣትም አልቻሉም።

ሶስት የሃሮማያ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በፌደራል ፖሊስ መኪና ተገጭተው ህይወታቸው አለፈ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሟች ተማሪዎች በባጃጅ መኪና ሲጓዙ እንደነበር የገለጹት ተማሪዎች፣ የፌደራል ፖሊስ መኪና የተደሳፈሩበትን ባጃጅ መኪና ገጭቶ እንደገደላቸው  ታውቋል።

አንደኛው ተማሪ ሆስፒታል ከገባ በሁዋላ መሞቱንና አስከሬኑ ወላጆቹ ወደሚገኙበት አዳማ ተልኳል። ሁለቱ ተማሪዎች በዚህ አመት የሚመረቁ ነበሩ። ድርጊቱ ሆን ተብሎ የተፈጸመ ይሁን ድንገተና አደጋ ለማወቅ አልተቻለም።

ሱዳን ሊቢያ ድንበር አቅራቢያ 300 ስደተኞችን ያዘች

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በሕገወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠው ወደ ግዛቴ ገብተዋል ያለቻቸውን 300 ስደተኞችን መያዝዋን ሱዳን አስታወቀች።

ስደተኞቹ የሳህራ በርሃን አቋርጠው ወደ ሊቢያ በመግባት በባሕር ወደ አውሮፓ ለማቅናት ሲጓዙ እንደነበር የሱዳን ልዩ ጦር የጸጥታ ሹም ጄኔራል መሃመድ ሃምዳን ገልጸዋል። በሰሜናዊ ሱዳን አል ሸቨርሊት ከተያዙት ስደተኞች ውስጥ አብዛሃኞቹ ኢትዮጵያዊያንና ኤርትራዊያን መሆናቸውንም አስታውቀዋል።። የሱዳን መንግስት በቅርቡ ከአውሮፓ ኅብረት የሕገወጥ ስደተኞችን ፍልሰት ለመቆጣጠር 100 ሚሊዮን ዩሮ እርዳታ እንዳገኘ ሱዳን ትሪቢውን አክሎ ዘግቧል።

ፍርድ ቤቱ የአቶ ሃብታሙ አያሌውን ጉዳይ ሳያየው ቀረ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በህመም በመሰቃዬት ላይ ባለው  የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው ላይ ጠ/ፍርድ የጣለበት ከአገር ውጭ የመጓዝ እገዳ ይነሳለታል ተብሎ ቢጠበቅም፣ ፍርድ ቤቱ ዳኛ አልተሟላም በሚል ውሳኔውን ለሌላ ጊዜ አስተላልፏል።

የአቶ ሃብታሙ ባለቤት ወ/ሮ ቤተልሄም አዛናው የፍርድ ቤቱን መልስ እንደሰማች ራሱዋን ስታ በመውደቋ ወደ ሆስፒታል ተወስዳለች።

የኢትዮጵያ ጦር የጋላድ ከተማን ለቆ ወጣ

ሰኔ ፳፰ ( ሃያ ስምንት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከፍተኛ የጦር መሳሪያ የታጠቁ የአልሸባብ ወታደሮች በማእከላዊ ሶማሊያ በጋለድቡ ክልል ውስጥ የምትገኘውን የጋላድ ከተማን ድጋሜ በቁጥጥር ስር አድርገዋል።

በስፍራው በአፍሪካ ኅብረት የሰላም አስከባሪ ስም የነበሩት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ወታደሮችና የሶማሊያ መንግስት የጸጥታ ኃይሎች ከተማዋን ለቀው መውጣታቸው ተዘግቧል።
የኢትዮጵያ ወታደሮች መሸሻቸውን ተከትሎ እኩለ ቀን ላይ የሶማሊያ የጸጥታ ኃይሎችና የከተማዋ አስተዳደሮች ሙሉ ለሙሉ እነሱን ተከትለው ከከተማዋ መውጣታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች እማኝነታቸውን ሰጥተዋል።

Monday, July 4, 2016

ኢትዮጵያዊ አርሶአደሮች 5 የሱዳን ወታደሮችን ገደሉ

በሰሜን ጎንደር ዞን በታች አርማጭሆ ወረዳ በሲናር በረሃ የኢትዮጵያን የእርሻ መሬት ለመውሰድ በተንቀሳቀሱ የሱዳን ወታደሮች ላይ ተኩስ የከፈቱት ኢትዮጵያዊ አርሶአደሮች 5 የሱዳን ወታደሮችን ገድለዋል።

ሰኔ 25 ቀን 2008 ዓም የሱዳን ወታደሮች የጓንግን ወንዝ ተሻግረውና አንድ የእርሻ ካም አቃጥለው ጦርነት ሲከፍቱ ፣ በተለይ  ጎዳና አምዴ  የተባለው ወ   ጣት አርሶአደር እና አብረውት የነበሩት 5 የሱዳን ወታደሮችን ገድለው 3 ክላሽንኮቭ እና አንድ መትረጊስ ማርከው  ወታደሮቹ እንዲሸሹ አድርገዋል።
የሱዳን  ወታደሮች ብዙዎችን ወታደሮች የገደለውን ወታት ጎዳናን ከመሸገበት ቦታ ሲወጣ ጠብቀው በመተኮስ ገድለውታል።     ይሁን እንጅ  የወጣቱን አስከሬን  ለመውሰድ አለመቻላቸውንና የአካባቢው ህዝብ ጥቃቱን በማጠናከሩ ወታደሮቹ እንዲያፈገፍጉ ማድረጉን የሟች ዘመዶች ገልጸዋል ።

የኮንሶ ህዝብ ጥያቄ ውድቅ መደረጉን ተከትሎ በአካባቢው ውጥረት ሰፍኗል

የደቡብ ክልል የብሄረሰቦች ምክር ቤት ሰኔ 23 ቀን 2008 ዓም የኮንሶ ህዝብ የራስ አስተዳደር ጥያቄ ውድቅ መደረጉን የሚግልጽ ደብዳቤ መጻፉን ተከትሎ በአካባቢው ውጥረት መንገሱን ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

ምክር ቤቱ በደብዳቤው “ የክልሉ ህገመንግስት አንቀጽ 59 ንኡስ አንቀጽ 3 እና የብሄረሰቦች ምክር ቤትን ለማጠናከር ስልጣንና ተግባሩን ለመዘርዘር የወጣው አዋጅ ቁጥር 60/95 መሰረት አጠቃላይ የጥያቄው ይዘትና ምክንያቶችን መርምሮ በማየት የኮንሶ ህዝብ መሰረታዊና ቀጥተኛ ጥቅሞችንና ሌሎች ህገመንግስታዊ አላማዎችን ለማሳካት እንዲቻል ህዝቡ አሁን ባለበት በሰገን አካባቢ ህዝቦች ዞን እንዲቀጥልና  ለብቻው ለብቻው በዞን ለመደራጀት ያቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት እንደሌለው በሰኔ 20/2008 ዓም በሃዋሳ የተካሄደው 3ኛው ዙር 3ኛ የስራ ዘመን 6ኛ መደበኛ ጉባኤ ውሳኔውን አሳልፏል፡” ሲል ጥያቄውን ላቀረቡት የኮንሶ ተወላጆች ገልጿል።

በአዲስ አበባ ቤታቸው የፈረሰባቸውን ሰዎች አሳዛኝ ህይወት የሚያሳዩ ፎቶግራፎች እየወጡ ነው

በወረዳ አንድ የሁለት ፖሊሶችንና የአንድ ወረዳ አስተዳዳሪን ህይወት ጨምሮ፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ዜጎች የተገደሉትን የቤት ማፍረስ ዘመቻ ለመደበቅ መንግስት ጥረት ቢያደርግም ቤታቸው የፈረሰባቸውን ዜጎች ህይወት የሚያሳዩ ፎቶዎች በማህበራዊ ሚዲያዎች እየተለቀቁ ነው።

የፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን አጥረው ምንም ሰው ወደ ውስጥ እንዳይገባ ጥረት ሲያደርጉ ሰንብተዋል። ይህን ተከትሎም አሽከርካሪዎች በመንገድ መጨናነቅ ሲቸገሩ ሰንብቷል። ነዋሪዎች እንደሚሉት መስተዳድሩ ድርጊቱ እንዳይታወቅበት ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል። ሆኖም የመስተዳድሩ አስከፊ እርምጃ ከመጋለጥ አላመለጠም።

በገላና ወረዳ አንድ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪ ተደበደበ

በሁሌ ቦራ ዞን በገላና ወረዳ ሜጄ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑትና ሰማያዊ ፓርቲን በመወከል ባለፈው ግንቦት ወር ምርጫ እጩ ተወዳዳሪ የነበሩት  አቶ ደስታ ቁጤ ከምሽቱ አንድ ሰአት ላይ በተፈጸመባቸው ድብደባ በእግሮቻቸው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶአቸው በህክምና እየተረዱ ነው።

ማንነታቸው ያልታወቁት ግለሰቦች ጨለማን ተገን አድርገው ግለሰቡን መደብዳበቸውንና ከዚህ ቀደም ከደህንነቶች ማስፈራሪያ ሲደርሰው እንደነበር እንደነገሯቸው የዞኑ የሰማያዊ ፓርቲ ተወካይ አቶ ጌታቸው በቀለ ለኢሳት ተናግረዋል

Friday, July 1, 2016

በአዲስ አበባ ከተማና አካባቢው ዜጎችን ከቤት ንብረታቸው የማፈናቀል ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ጠየቀ

ኢሳት (ሰኔ 24 ፥ 2008)

በአዲስ አበባ ከተማና አካባቢው ዜጎችን ከቤት ንብረታቸው የማፈናቀል ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ጠየቀ።
ዜጎች ለረጅም ዓመታት በይዞታነት ግብር ሲከፍሉበት ከቆዩበት ቦታ “ህገወጥ ናችሁ” ብሎ ማፈናቀል በምንም መልኩ ተቀባይነት ያለው ድርጊት አለመሆኑን ድርጅቱ ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል።
በቦሌ ክ/ከተማ ወረገኑ የሚባል አካባቢን ጨምሮ በተለያዩ ክፍለከተሞችና በአዲስ አበባ ከተማ ዳርቻ ለረጅም ጊዜ ከኖሩበት ቦታ በአፍራሽ ግብረሃይል ቤቶችን ማፍረስ አግባብ አለመሆኑን ሰመጉ በሪፖርቱ ላይ ጠቅሷል። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ ቀርሳና ኮንቶማ 19ሺ 246 ነዋሪዎች በቤት ማፍረሱ ሂደት እንደተፈናቀሉ ተገልጿል። በተመሳሳይ መልኩ፣ በተክለሃይማኖት ከ250 በላይ አባዎራዎች ለብዙ አመታት ከኖሩበት ቦታ ለቃችሁ ውጡ መባላቸውን ለሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ መናገራቸው በሰመጉ ሪፖርት ላይ ሰፍሯል። በኢርቱ ተክለሃይማኖት እንዲሁ 169 የቤተሰብ ሃላፊዎች ለአመታት ከኖሩበት ቦታ በመፈናቀላቸው በከፍተኛ ችግር ላይ መሆናቸው ተነግሯል።

በአቶ ሃብታሙ አያሌው ላይ በፍርድ ቤት የተጣለበት እገዳ እንዲነሳ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ጥሪ አቀረበ

ኢሳት (ሰኔ 24 ፥ 2008)

በፍርድ ቤት ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ እገዳ ተጥሎበት የሚገኘውና በጽኑ ህመም ላይ የሚገኘው የአንድነት ፓርት አመራር አቶ ሃብታሙ አያሌው የተጣለበት እገዳ እንዲነሳለት አምነስቲ ኢንተርናሽናል ጥሪውን አቅረበ።
የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ለጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ በላከው የጽሁፍ መልዕክት አቶ ሃብታሙ ከሰብዓዊ መብት አንጻር እገዳው በአስቸኳይ ሊነሳለት የሚገባ እንደሆነ አመልክቷል።
በእስር ቤት ቆያታው የተለያዩ ስቃዮች በአቶ ሃብታሙ አያሌው ላይ ሲፈጸምበት መቆየቱን ያወሳው አምነስቲ ኢንተርናሽናል በማዕከላዊ የምርመራ እና የቂሊንጦ እስር ቤቶች የነበረው ቆይታው ለጤናው መታወክ ምክንያት መሆኑን አክሎ ገልጿል።