Tuesday, February 9, 2016

በእስር ላይ የሚገኙ የፓርቲ አመራሮች በፍርድ ቤት ቀጠሮ እየተሰቃዩ ነው

የካቲት ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት በተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ነጻ ያላቸውና አቃቤ ሕግ ይግባኝ በመጠየቁ ምክንያት በጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ጉዳያቸው በመታዬት ላይ ያሉት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሽ እና መምህር አብርሃም ሰሎሞን ዛሬ የካቲት 01 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቢቀርቡም ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ወደ እስር ቤት ተመልሰዋል።  
አቃቤ ሕግ በአቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ ላይ የሚቀርበው ከብሔራዊ ደኀንነትና መረጃ ማዕከል ተገኘ የተባለው ኦርጂናል ማስረጃ ያቀርባል ተብሎ ቢጠበቅም፣ ማስረጃውን ለማቅረብ ተጨማሪ የአንድ ...ሳምንት ጊዜ እንዲሰጠው በጽሁፍ ጠይቋል።
ከብሔራዊ ደኀንነትና መረጃ ማዕከል የግለሰቦቹን የመልዕክት ልውውጥ በሚያሳይ መልኩ ተስተካክሎ እንዲቀርብለት አቃቤ ሕግ ቢጠይቅም፣ በስራ ጫናና መደራረብ ምክንያት በተጠየቀው ቀን ማድረስ እንደማይቻል ምላሽ እንደተሰጠው ለፍርድ ቤት ጠቅሶ ተለዋጭ ቀጠሮ መጠየቁን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል።
የፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ የመልዕክት ልውውጥ በሚያሳይ መልኩ ተስተካክሎ እንዲቀርብ ሳይሆን ቀጥታ ኦርጅናሉ እንዲቀርብ መሆኑን በማስታወስ ፍርድ ቤቱ ይህን እንዲገነዘብላቸው ተከሳሾቹ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱም የተከሳሾችን ማስታወሻ ተቀብሎ እስከ የካቲት 7 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርብ ሲል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ የሚገኙት አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታና አቶ ዳንኤል ሺበሽ በማረሚያ ቤቱ አስተዳደር በኩል በደል እየተፈጸመብን ነው ሲሉ አቤቱታቸውን ያሰሙ ሲሆን፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ በጨለማ ቤት ውስጥ መታሰሩንና ቤተሰቡን ለማዬት አለመቻሉን እንዲሁም ከውጭ ምግብ እንዳይደርሰው መደረጉን አስረድቷል።
አቶ የሽዋስ አሰፋ በበኩሉ ለሰባት ወሮች ያክል ቤተሰቦቹን እንዳያይ መከልከሉን ተናግሯል። አብርሃ ደስታም ተመሳሳይ የመብት ጥሰት እየተፈጸመበት መሆኑን ገልጽዋል።
የሶስቱን ተከሳሾች አቤቱታ ፍርድ ቤቱ መዝግቦ፣ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ለየካቲት 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀርቦ መልስ እንዲሰጥ ትእዛዝ መስጠቱን ጋዜጣው ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment