Tuesday, February 16, 2016

ከእስር እንዲፈቱ ከወሰነላቸው አምስት የፓርቲ አመራሮችና አባላት መካከል ሁለቱ ብቻ ማክሰኞ ተፈቱ

ኢሳት (የካቲት 8 ፥ 2008)
የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የይግባኝ ጥያቄ ቀርቦባቸው ከእስር እንዲፈቱ ከወሰነላቸው አምስት የፓርቲ አመራሮችና አባላት መካከል ሁለቱ ብቻ ማክሰኞ ተፈቱ።
...
ፍርድ ቤቱ ከቀናት በፊት ሁሉንም ተከሳሾች ከእስር ቤት እንዲለቀቁ ወስኖ የነበረ ሲሆን፣ የአንድነት የህዝብ ግንኙነት አቶ ሃብታሙ አያሌውና በተመሳሳይ ክስ ስር የነበረው መምህር አብርሃም ሰለሞን ከእስር መለቀቃቸው ታውቋል።
ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ሳምንት አርብ ሁሉም ተከሳሾች ከእስር ቤት እንዲወጡ ቢወሰንም የቃሊቲ እስር ቤት ተከሳሾቹ ችሎት በመድፈር የተላለፈባቸውን ቅጣት ስላልጨረሱ ሊለቀቁ አለመቻላቸውን መግለጹ ይታወሳል።
ይሁንና፣ ተከሳሾቹ ቅጣታቸውን እንደጨረሱ ቢገልፅም የእስር ቤቱ ሃላፊዎች ቅጣቱ እጃቸው ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ የሚቆጠር አይደለም በማለት ቅጣቱ አለማለቁን ለፍርድ ቤት ገልጿል።
በመኢአድና የአረና ፓርቲ ውስጥ በተለያዩ ሃላፊነቶች ውስጥ ሲያገለግሉ የነበሩ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋና፣ የአረናው ፓርቲ አመራር አብርሃ ደስታ ከእስር እንዲለቀቁ ቢወሰንላቸውም፣ አለመለቀቃቸውን ከሃገር ቤት የተገኘ መረጃ አመልክቷል።
ሶስቱ ተከሳሾች ሊለቀቁ ያልቻለው ችሎት በመድፈር ጋር ተላልፎባቸው በነበረው ቅጣት ጋር በተገናኘ ይሁን አይሁን የታወቀ ነገር የለም።
ከአንድ አመት በፊት ለእስር ተዳርገው የነበሩ አምስት ተከሳሾች በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በነጻ እንዲሰናበቱ ቢወሰንላቸውም፣ ከሳሽ አቃቤ ህግ ውሳኔውን በመቃወም ይግባኙን ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ማቅረቡ ይታወሳል።
አቃቤ ህግ ተከሳሾችን በውጭ ሃገር ካሉ ሃይሎች ጋር በመተባበር ህገ-መንግስቱን በሃይል ለመናድ ተንቀሳቅሰዋል ሲል በሽብር ወንጀል መክሰሱ የሚታወቅ ነው።
ይሁንና ጉዳዩን ሲመለከት የቆየው የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተከሳሾች ራሳቸውን መከላከል አያስፈልጋቸውም ሲል ከሰባት ወር በፊት በነጻ አሰናብቶ የነበረ ሲሆን ከሳሽ አቃቤ ህግ ያቀረበውን ይግባኝ ተከትሎ ተከሳሾች በእስር ቆይተዋል።

No comments:

Post a Comment