Friday, February 5, 2016

አራቱ የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን በጠቅላይ ፍርድ ቤት ከዐቃቤ ሕግ ጋር የቃል ክርክር አደረጉ

ዐ/ሕግ በጥቅምት ወር 2008 በፌ/ከ/ፍ/ቤት የሽብር ክሳቸው ተነስቶላቸው የተሰናበቱት አምስቱ ጦማሪያን ላይ «ማስረጃችን አልተመዘነም፣ በተከሰሱበት ወንጀል ሊከላከሉ ይገባል» በማለት ለፌ/ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ማለቱ ይታወሳል። በዛሬው ዕለት ጥር 27፣ 2008 አራቱ መልስ ሰጪዎች በፍቃዱ ኃይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፉ ብርሃኔ እና አቤል ዋበላ ከጠበቆቻቸው አምሀ መኮንን እና ሽብሩ በለጠ ጋር ቀርበው ለይግባኙ መልስ ሰጥተዋል።
ይግባኝ ባይ በስር ፍ/ቤት «ከመጀመሪያ ጀምሮ የቡድኑን ሥም ካልገለጻችሁ እያተባልን፣ የቡድን አደረጃጀት ገልጸን አልገለጻችሁም እየተባልን ማስረጃዎቻችን አልታዩልንም። 1ኛ መልስ ሰጪ ቤት የግንቦት 7 እና የኦነግ ፕሮግራም ተገኝቷል። ቡድኑ የግብፅን አብዮት ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት የሠለጠኑበት የተለያዩ ሰነዶች ተያይዘዋል። 2ኛ መልስ ሰጪ አመፅ ሊያነሳሳ ማሰቡን አምኗል፣ የቀረቡበት ማስረጃዎችም ይህንኑ ያስረዳሉ በሚል በወንጀል ሕጉ 257/ሀ መሠረት ይከላከል ከማለቱ በቀር በጥቅሉ መልስ ሰጪዎች በቡድን ‘እንዴት የግብፅን ዓይነት አብዮት ኢትዮጵያ ውስጥ መቀስቀስ ይቻላል?’ በሚለው ላይ የተጻጻፏቸውን፣ እና የወሰዱትን ሥልጠና የሚያስረዱ በርካታ ሰነዶች ተይዘዋል። ከያንዳንዳቸው ኮምፒዩተሮች የወጡት ሰነዶች የሚያስረዱት፣ እንዴት አመፅ ማነሳሳት እንደሚቻል ነው። አንዱ መልስ ሰጪ ላይ በእጅ ጽሑፉ እንዴት ፈንጂ ማላቆጥ እንደሚቻል የሚገልጽ
ጽሑፍ ተገኝቷል። ስለሆነም ማስረጃዎቼ በስር ፍ/ቤት አልታየልኝም፣ በመጀመሪያው ክስ ይከላከሉ።» ብሏል።
የመልስ ሰጪ ጠበቆች በበኩላቸው በአቶ አምሀ አማካይነት ይግባኝ ባይ መልስ ሰጪዎች ላይ የመሠረተው “የሽብር ወንጀል ለመፈፀም አቅዳችኋል፣ አሲራችኋል፣ ተንቀሳቅሳችኋል የሚል ክስ ሲሆን ከመጀመሪያ ጀምሮ 15 የክስ መቃወሚያ አቅርበናል። ይግባኝ ባይ የመጀመሪያ ገፅ ላይ መልስ ሰጪዎችን የሥራ ድርሻ ግለጽ ተብሎ መግለጽ ባለመቻሉ ብቻ ከሦስት ወር በኋላ ፍሬ ነገሩ ከክሱ እንዲወጣ ተበይኗል። ፍሬ ነገሩ ከክሱ ባይወጣም ኖሮ ዳኞች ይሄ ስላልተገለጸ ብለው ያሳለፈው ብይን የለም። የቡድን ሥም የተባለውም፣ ከተቻለ የቡድኑን ሥም ካልተቻለ ከሌሎች የሚለይበትን ነገር አቅርብ ተብሎ ዐ/ሕጉ ግን ‘የዞን ዘጠኝ የጦማሪያን እና አራማጆች ስብስብ’ የሚለውን ማቅረብ ስላልቻለ ሳይሆን ስላልፈለገ ባያቀርብም ዳኞች ቡድኑ አሁን ከሌሎች ተለይቷል ብለው ለነሱ ፈርደዋል። ቡድኑ በፓርላማ አልተፈረጀም ስንልም ለነበረው ተመሳሳይ ሥልጣን በሽብር አዋጁ ለፍ/ቤቱም ተሰጥቶታል በሚል የተፈረደው ለነሱ ነው።
«ነገር ግን በኋላ ላይ ቡድኑ እንኳን ለሽብር ለተራ ወንጀል እንኳ አልተደራጀም በሚል ፍ/ቤቱ ትክክለኛ ብይኑን አሳልፏል። 2ኛ መልስ ሰጪ በስር ፍ/ቤት እየተከላከለ ባለበት ሁኔታ በሥነ ስርዓት ሕጉ 181 መሠረት በተመሳሳይ ጉዳይ ይግባኝ ሊባልበት አይገባም። 3ኛ መልስ ሰጪ ኢሜይል ውስጥ የተገኘው የግንቦት ሰባት ኒውስሌተር፣ የሽብር አዋጁ ሳይወጣ የተላከ ከመሆኑም በላይ መልስ ሰጪ ጠይቆ የተላከለት ወይም ሲደርሰው መልስ የሰጠበት ነገር አይደለም። ግንቦት 7 መንግሥትን ይቃወማል፣ ሌሎችም ይቃወማሉ። ሌሎች ሰዎች መንግሥትን ስለተቃወሙ ብቻ የግንቦት 7ን ሁለንተናዊ የትግል ስትራቴጂ ተቀብለዋል ማለት ግን አይቻልም። መልስ ሰጪዎች የሽብር ወንጀል ለመፈፀም አቅደው አሲረዋል ሲል ከአንቀፅ 4 በመነሳት አንቀፅ 3/2ን ጠቅሶ ‘የማኅበረሰቡን ጤና እና ደኅንነት አደጋ ላይ ለመጣል’ አሲረዋል ብሎ ሲወነጅላቸው ዐ/ሕግ ያቀረበው የጻፏቸውን ጽሑፎች ብቻ በመሆኑ እና መልስ ሰጪዎች ላይ አንድም ቀጥተኛ ምስክር ስላልቀረበባቸው ነጻ መባላቸው ተገቢ ነው።
«በተደጋጋሚ የተጠቀሱትን ሥልጠናዎች በተመለከተ የት፣ መቼ፣ ስለምን፣ በነማን ተሰጠ የሚለውን ዐ/ሕግ መግለፅ አይፈልግም። ይህን ማድረግ ባልቻለበት ሁኔታ አስረድተናል እያለ ነው። ሥልጠና ከሚባሉት አንዱ ሴኩሪቲ ኢን ኤ ቦክስ በሚል ማንኛውም ሰው ሊወስደው የሚገባ የደኅንነት አጠባበቅ ሥልጠና ነው። ከሦስተኛ ወገን የራስን ምስጢር መጠበቅ በሕገመንግሥቱ የተረጋገጠ መብት ነው። በተጨማሪም፣ ፈንጂ መላቆጥ ሠልጥነዋል የተባለው ጭራሹኑ የሥልጠናውን ዓይነት ያላገናዘበ ነው። ሥልጠናው ጋዜጠኞችና ጦማሪያን አስቸጋሪ ቦታዎች ላይ ዘገባ ሲያደርጉ ደኅንነታቸውን እንዴት መጠበቅ እንዳለባቸው የሚያስረዳ ነው። ጋዜጠኞች አመፅ የተከሰተባቸው ቦታዎች ላይ ተገኝተው የሚዘግቡ ከሆነ አመፀኞቹ ምን ዓይነት መሣሪያ ሊጠቀሙ ይችላሉ የሚለውን በጨረፍታ ለማሳወቅ የተገለጸውን ነው ፈንጂ ማላቆጥ ተምረዋል የሚለው። ይህንን ራሳቸው መልስ ሰጪዎች ቢያስረዱት ይሻላል» ብለዋል። ይሁን እንጂ ዳኞች ዕድሉን ለመልስ ሰጪዎች ሳይሰጡ ቀርተዋል።
አቶ አምሀ በተናገሩት ላይ የጨመሩት አቶ ሽብሩ «ይግባኝ ባይ ያቀረበው ማስረጃ እና በቃሉ የሚናገረው አይገናኙም። ለምሳሌ ማስረጃ ከተባሉ ሰነዶች መካከል ናትናኤል ፈለቀ የሀይስኩል ተማሪ እያለ የጻፈው ግጥም ማስረጃ ተብሎ ቀርቧል። የሰነድ ማስረጃ የሚባሉት እንዲህ ዓይነት ናቸው።» ብለዋል።
በዚሁ ለብይን መጋቢት 20፣ 2008 ቀጠሮ ተይዟል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በ‘አመጽ ማነሳሳት ወንጀል’ ራስህን ተከላክለህ ነጻ ውጣ የተባለው በፍቃዱ ኃይሉ ሰኞ መከላከያ ምስክሮቹን በፌ/ከ/ፍ/ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ሰኞ ጥር 30፣ 2008 ያስደምጣል።

No comments:

Post a Comment