Tuesday, February 16, 2016

በሚዛን ቴፒ በትንሹ 15 ሰዎች በመኪና አደጋ መሞታቸውን ፖሊስ ገለጸ

ኢሳት (የካቲት 8 ፥ 2008)
በደቡብ ክልል ከሚዛን ወደ ቴፒ ከተማ ይጓዝ የነበረ የሚዛን ቴፒ ዩንቨርስቲ አውቶቡስ የመገልበጥ አደጋ ደርሶበት በትንሹ 15 ሰዎች መሞታቸውን ፖሊስ ማክሰኞ አስታወቀ። ...
በዚሁ አደጋ 32 ሰዎች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፣ ተጎጂዎቹ ከሚዛን ወደቴፒ ከተማ ተጉዘው የብቃት ማረጋገጫ ፈተና ወስደው ሲመለሱ አደጋው መደረሱን ፖሊስ ገልጿል።
የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርስቲ ሰራተኞችን ይዞ ይጓዝ የነበረው አውቶቡስ በቁ በሚባል ወንዝ ውስጥ በመግባቱ አሰቃቂው አደጋ ሊደርስ መቻሉን እማኞች አስረድተዋል።

በአደጋው ጉዳት የደረሰባቸው ከ30 በላይ መንገደኞችም በቴፒ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው ሲሆን፣ ከ15ቱ ሟቾች መካከልም አንድ ህጻን እንደሚገኝበት ፖሊስ አክሎ ገልጿል።
ባለፈው ሰምንት ደርሰው በነበሩ ሁለት የተሽከርካሪ አደጋዎች 36 ሰዎች መሞታቸው የሚታወስ ሲሆን፣ በሃገሪቱ እያደረሰ ያለው የትራፊክ አደጋም ከምቼውም ጊዜ በላይ እየጨመረ መምጣቱን የትራንስፖርት ሚኒስቴር አመልክቷል።
የአሮጌ ተሽከርካሪዎች መብዛት፣ የትራፊክ ምልክት በአግባቡ አለመኖር፣ ጠጥቶና ጫት ቅሞ ማሽከርከር ለጉዳቱ ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸው ይነገራል።
የአለም ጤና ድርጅት በበኩሉ ኢትዮጵያ ካላት የህዝብ ቁጥር አንጻር አነስተኛ ተሽከርካሪ ቢኖራትም እየደረሰ ያለው ጉዳት ግን በአለም ደረጃ ከፍተኛ መሆኑን አስታውቋል።
ከ90 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ባላት ኢትዮጵያም የተሽከርካሪዎች ቁጥር አንድ ሚሊዮን የማይሞላ ሲሆን፣ ባለፈው አመት ብቻ ከሶስት ሺ በላይ ሰዎች በዚሁ አደጋ መሞታቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።

No comments:

Post a Comment