Tuesday, December 8, 2015

ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ባለፈው ግንቦት ወር ተካሂዶ በነበረው ምርጫ እንዲሳተፉ ጥሪ ቀርቦላቸው እንደነበር አና ጎሜዝ ተናገሩ

ኀዳር ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢህአዴግ በአሸባሪነት የሚፈርጃቸው የአርበኞች ግንቦት7 ሊቀመንበር ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ግንቦት ወር ተካሂዶ በነበረው ምርጫ እንዲሳተፉ፣ በእርሳቸው በኩል መልክት እንዲያስተላልፉ ተነግሮአቸው እንደነበር የአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባል እና የኢትዮጵያ የምርጫ 97 የህብረቱ የምርጫ ታዛቢ ልኡካን መሪ ሚስ አና ጎሜዝ ተናግረዋል።

ሚስ አና ጎሜዝ ይህን የተናገሩት ባለፈው ሳምንት ተዘጋጅቶ በነበረው ስብሰባ ላይ ነው። መንግስት በአንድ በኩል ፕ/ር ብርሃኑን ሽብረተኛ ይላቸዋል፤ በሌላ በኩል ደግሞ ወደ አገር ተመልሶ በምርጫው እንዲሳተፍ መልእክት እንዳስተላልፍላቸው ጠይቀውኝ ነበር፣ ያሉት አና ጎሜዝ፣ መልእከቱን ማድረሳቸውንና ፕሮፌሰሩ መሰረታዊ የሚባሉት ጥያቄዎች ከተሟሉ በምርጫው ለመሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውን መልስ እንደሰጧቸው ተናግረዋል። ይሁን እንጅ አሉ ባለስልጣኑዋ፣ መመለስ አለባቸው የተባሉት መሰረታዊ ጥያቄዎች ባለመመለሳቸው ኢህዴግ ምርጫውን 100 በመቶ አሸንፍኩ በማለት አስደምሞናል ብለዋል።
ሚስ አና የሽምግልና ጥያቄው የቀረበላቸው እርሳቸው የአፍሪካና ካረቢያን አገራት የፓርላማ አባላት ስብሰባ ለመካፈል ወደ አዲስ አበባ ባቀኑበት ወቅት ነው። ኢሳት በወቅቱ ዘገባውን ያቀረበ ቢሆንም፣ ጥያቄው በአንድ የአውሮፓ ዲፕሎማት መቅረቡን ከመግለጽ ውጭ የዲፕሎማቷን ስም አልጠቀሰም ነበር።

No comments:

Post a Comment