Thursday, December 10, 2015

የፌደራል ፖሊሶችና የመከላከያ አባላት ሰላማዊ ተቃውሞ በሚያደርጉ ዜጎች ላይ ከባድ እርምጃ ወሰዱ

ኀዳር ፴ (ሠላሳ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በወሊሶ ላለፉት አምስት ቀናት ሲካሄድ የነበረው ተቃውሞ ተጠናከሮ የቀጠለ ሲሆን፣ ከሰአት በሁዋላ የፌደራል ፖሊስ አባላት እርምጃ መውሰድ ጀምረዋል። በሰላማዊ ዜጎች ላይ በቀጥታ በመተኮስ በርካታ ቁጥር ያላቸው ነዋሪዎች ቆስለው ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል። እስካሁን አንድ ሰው መሞቱን ለማወቅ ቢቻልም፣ በሞትና በህይወት መካከል ያሉ በርካታ ወጣቶችና አዛውንቶች ሳይቀር መኖራቸው ታውቋል።

ነዋሪዎቹ የውስጥ ለውስጥ መንገዶችንና ወደ ጅማ የሚወስደውን አውራ ጎዳና በመዝጋት ሲቃወሙ አርፍደዋል። ጥቃት የተፈጸመባቸው ወደ ዞን አስተዳደር ጽ/ቤት ሲያመሩ መሆኑን የአይን እማኞች ገልጸዋል።
የጸጥታ ሃይሎች የሚወስዱት እርምጃ ተቃውሞውን ሊያቆመው ባለመቻሉ፣ የፌደራል ፖሊሶችን በብዛት የጫኑ መኪኖች ወደ ወሊሶ ተንቀሳቀስዋል።
በምእራብ ወለጋ በዋንጆ ከተማ አያና በንቲና ሉጫ ገመቹ እንዲሁም በአናጎ ከተማ አላዘር ቀልቤሳ መገደላቸው የታወቀ ሲሆን በምእራብ ሰዋ ጨሌዋ ወረዳ የጌዶ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ የሆነው ፈቃዱ ግርማም እንዲሁ ተገድሏል። በርካታ ሰዎች ቆስለው ሆስፒታል መግባታቸውም ታውቋል። በአርሲ ነገሌም እንዲሁ በህዝቡ ላይ ጥቃት መፈጸሙን መረጃዎች ደርሰውናል። ከአዲስ አበባ በ40 ኪሜ ርቀት ላይ በምትገኘዋ የሰንዳፋ ከተማ ዛሬ ከሰአት በሁዋላ ህዝቡ ሆ ብሎ በመውጣት መንገዶችን በመዝጋት ተቃውሞውን ገልጿል። በምእራብ ሸዋ ባቢች ከተማም ህዝቡ የጸጥታ ሃይሎችን ከከተማዋ አስወጥቷል።
በጉጂ ዞን በቦሬ ወረዳ የቦሬ አንደኛ ደረጃ፣ ሁለተኛ ደረጃና የመሰናዶ ተማሪዎች ተቃውሞ የቀጠለ ሲሆን፣ ፖሊሶች ከ30 ያላነሱ ተማሪዎችን ይዘው አስረዋል።በጅማ ዩኒቨርስቲ ፉርዲሳ ግቢ ፖሊሶች በተማሪዎች ላይ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ለመበተን ሞክረዋል።
በደቡብ ክልል በዲላ ዩኒቨርስቲ ደግሞ ህዳር 28 ከምሽት 2 ሰአት ተኩል ላይ በኦሮሞ ተማሪዎች ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በሁዋላ፣ የአካባቢው ሹሞች የደቡብና የኦሮሞ ተማሪዎችን ለማጋጨት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የግቢው ምንጮች ግልጸዋል። ባለስልጣናቱ ጥቂት የስርዓቱ ደጋፊ ተማሪዎች በኦሮሞ ተማሪዎች ላይ የተቃውሞ ሰልፍ እንዲወጡ እያዘጋጁዋቸው ነው። እስካሁን ከ100 በላይ የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ታስረዋል፡፡

No comments:

Post a Comment