Saturday, December 12, 2015

በድርቅ የተጎዱና የተረጂዎች ብዛት 18 ሚሊዮን ደርሷል ተባለ

በድርቅ ሳቢያ ለረሃብ የተጋለጡ ኢትዮጵያዊያን ከአስር ሚሊዮን በላይ እንደሆነ በመጥቀስ በይፋ የእርዳታ ጥሪ የቀረበ ሲሆን፤ የተረጂዎች ጠቅላላ ቁጥር 18 ሚሊዮን እንደደረሰ ተገለፀ፡፡
የድርቁ አደጋ ከባድ መሆኑን በመግለጽ ለቀረበው የእርዳታ ጥሪ ፈጣን ምላሽ እንደሚያስፈልግ የተናገሩት የእንግሊዝ የውጭ ተራድኦ ሚኒስትር፤ በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ድጋፍ የሚያገኙት 7.9 ሚሊዮን ሰዎችን ጨምሮ የተረጂዎቹ ቁጥር 18 ሚሊዮን ሆኗል ብለዋል፡፡
በድርቁ ተጎጂ የሆኑ ዜጎች በጥር ወር ወደ 10.2 ሚሊዮን እንደሚያሻቅብ መንግስት ይፋ ያደረገ ሲሆን ለመጀመሪያው ዙር እርዳታ 516 ሺህ ሜትሪክ ቶን የምግብ እርዳታ ያስፈልገኛል ብሏል፡፡ መንግስት ለለጋሽ ሀገራትና ተቋማት የእርዳታ ጥሪ በይፋ አቅርቧል፡፡
ለምግብ ግዢ ብቻ 1.1 ቢሊየን ዶላር እንደሚያስፈልገው የጠቀሰው መንግስት፤ አጠቃላይ የድርቁን ችግር ለመቋቋም ከ1.4 ቢሊየን ዶላር በላይ ገንዘብ እንደሚያስፈልገው አስታውቋል፡፡
በትግራይ የድርቁ ተጎጂዎች 1.2 ሚሊዮን፣ በአማራ ክልል 2.3 ሚሊዮን፣ በአፋር 409,200፣ በኦሮሚያ 3.8 ሚሊዮን፣ በደቡብ ክልል 668,900፣ በሱማሌ 1.5 ሚሊዮን፣ በድሬደዋና በሐረሪ በድምሩ ከ80 ሺህ በላይ፣ በጋምቤላ 37 ሺህ 450 እንዲሁም በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል 83,476 መሆናቸውን የመንግሥት ሪፖርት አመልክቷል፡፡
ለድርቁ የውጭ ሀገራት ለጋሽ ድርጅቶችና ተቋማት ድጋፍ እንዲቸሩት በትናንትናው እለት መንግስት ጥሪ ያቀረበ ሲሆን ከ50 በላይ ለሚሆኑ ዲፕሎማቶችና አለማቀፍ ለጋሽ ተቋማት ስለድርቁ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡
ከድርቁ ጋር በተያያዘ ከ400 ሺህ በላይ ህፃናት አስቸኳይ አልሚ ምግብ ይፈልጋሉ ያለው መንግሥት፤ 3.6 ሚሊዮን ዜጎች ደግሞ ድርቅ አምጪ በሆኑ የተለያዩ በሽታዎች ሊጠቁ እንደሚችል ሪፖርት አድርጓል፡፡  ድርቁ በአጠቃላይ 429 ወረዳዎች የተከሰተ ሲሆን 286 ሺህ 400 ሰዎችን ሊያፈናቅል ይችላል ተብሏል፡፡

No comments:

Post a Comment