Tuesday, December 8, 2015

የሰቆጣ አርሶ አደሮች እየተሰደዱ ነው

ኀዳር ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በኢትዮጵያ የሚታየውን ከፍተኛ ረሃብ ተከትሎ መንግስት አርሶ አደሩ ቀየውን እንዳይለቅ ከፍተኛ ጥበቃ እያደረገ ቢሆንም፣ አርሶአደሮች ግን በሌሊት እየጠፉ በመሰደድ ላይ ናቸው። በፎቶ ግራፍ የተደገፉ መረጃዎች እንደሚያሳዩት የሰቆታ አርሶአደሮች በቡድን በቡድን በመሆን ወደ ጎንደር የተለያዩ ከተማዎች ተሰደዋል። በሊቦ ከምከም ወረዳ በአዲስ ዘመን እና ይፋግ ከተማዎች በርካታ ስደተኞች የገቡ ሲሆን፣ የአካባቢው ነዋሪዎችም ተቀብለው እያስተናገዱዋቸው ነው።

በአማራ ክልል የድርቁ ስፋት እየጨመረ በመጣበት በአሁኑ ወቅት በርካታ ወጣቶች ‹‹ ከርሃብ ጦርነት ይሻላል ››ማለት መጀመራቸውን ወላጆች ተናግረዋል።
‹‹ መንግስት የተከሰተውን ድርቅ መቋቋም አልቻለም!›› የሚሉት ተጎጂዎች ፣ የሚቀርብላቸው ምግብ በቂ ባለመሆኑ አብዛኛው ተጎጂ በርሃብ እንዲሰቃይ በመደረጉ በተለይ ወጣቶች አካባቢያቸውን ለቀው በመሄድ መንግስትን ለመቃዎም እንቅስቃሴ ሊያደርጉ ይችላሉ › ሲሉ ወላጆች ተናግረዋል፡፡

‹‹ ረሃቡ ሲበረታ በቀጣይ ምን ሊመጣ ይችላል ብለን እየሰጋን ነው፡፡ ›› የሚሉት የችግሩ ተጎጅ ቤተሰቦች ‹‹ በቂ ያልሆነ የእርዳታ እህል በመላክ እርስ በርስ እንድንጨቃጨቅ እየተደረግን ነው ›› በማለት ወቀሳ አቅርበዋል።
መንግስት በቂ የእርዳታ እህል በማምጣት ከማከፋፈል ይልቅ፣ አንዱን ሰጥቶ አንዱን የሚነሳበት አካሄድ መታየቱ ህዝቡን በስርዓት ለማስተናገድ እንዳልቻለ የሚያሳይ መሆኑን የችግሩ ሰለባ የሆኑት ወላጆች ይናገራሉ፡፡
ወጣቶቹ ከእናት አባታችው እጅ ነጥቀው ከሚበሉ ወደ ተቃውሞ መሄድን እንደሚመርጡ አበክረው የሚናገሩት ወላጆች፣ ወጣቱ ተደራጅቶ ለመቃዎም እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ከረሃቡ የተነሳ አመጹ በቅርብ ሊከሰት ይችላል ሲሉ አክለዋል፡፡
‹‹ የገዢው መንግስት የሚያቀርበው እርዳታ ህዝቡን ያቀፈ አይደለም ›› የሚሉት ሌላው ተጎጅ አርሶ አደር፣ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በድርቁ ተጎድቶ እየታየ “ትሻላላችሁ” በመባል ርዳታ ለማግኘት አልቻሉም፡፡ስደት ከምትሄዱ ተቀመጡ የተባሉ አርሶአደሮች መኖራቸውንም ተናግረዋል።
ያሉንን ከብቶች በመሸጥ እህል ሸምተን እየበላን ነው የሚሉት ሌላው ተጎጂ አርሶ አደር ፣ የእህል ችግር በከፍተኛ ደረጃ በመከሰቱ ሌላ አማራጭ በማጣት ንብረታቸውን እየሸጡ ለጊዜው ነብሳቸውን ለማዳን ጥረት እያደረጉ መሆኑን በመናገር ከብቱም ሆነ ሰው የሚበላውና የሚጠጣው አጥቶ በመሰቃየት ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ከብቶቻቸውን ለመሸጥ እንኳን ገዢው መንግስት የተመቻቸ ነገር አለመፍጠሩን የሚናገሩት የችግሩ ሰለባዎች፣ በ6 ሽህ ብር ሲሸጥ የነበረውን ከብት ከ3 ሽህ ብር በታች፤በአንድ ሽህ ብር ሲሸጥ የነበረውን ፍየል ከ400 ብር በታች እየሸጡ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
አብዛኛው ወጣት ቀየውን ለቆ ወደ ጠረፍ ከተሞች ለስራ በመሄድ ላይ መሆኑን የሚናገሩት ተጎጂ አርሶ አደሮች፣ የእርዳታ እህል በማለት ያከፋፈሏቸው ለሰባት ሰው አስራ አምስት ኪሎ ብቻ በመሆኑ ነዋሪው አሁንም የችግሩ ሰለባ እንደሆነ ተናረዋል፡፡
በሌላ በኩል የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ከፍተኛ ድርቅ የተከሰተባቸውን የአፋር እና የሶማሌ ክልሎችን ለጋዜጠኞች ሳያስጎበኝ መቅረቱ ታውቋል።
ከ20 በላይ የመንግስትና በጣት የሚቆጠሩ የግል ፕሬሶችን ያቀፈ የጋዜጠኞች ቡድን ከ15 ቀናት በላይ በኦሮሚያ፣ አማራ፣ትግራይ፣ ደቡብ፣ ሀረሪ ክልሎች በመዘዋወር ለፕሮፖጋንዳ የተዘጋጁትን ሰዎችና ሹማምንት ቃለመጠይቅ ሲያደርግ ሰንብቶ እሁድ እለት ተመልሶአል።
ጋዜጠኞቹ በጉዞአቸው የድርቁ ችግር አስከፊ ደረጃ የደረሰባቸውን የአፋርና የሶማሌ ክልሎች እንዳይጎበኙ መደረጉ አሳዝኖአቸዋል። ጋዜጠኞቹ በተዘዋወሩባቸው ክልሎች ችግሩ አስከፊ ደረጃ ላይ መሆኑን መገንዘባቸውን፣ የመንግስትም ምላሽ እጅግ የዘገየና በአነስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ተረጂዎች ከብቶቻቸው ለሞት ሊዳረጉባቸው ግድ ሆኖአል። በአንዳንድ አካባቢዎች ከብቶቾቻቸውን እጅግ በርካሽ ዋጋ በመሸጥ ቤተሰባቸውን ለማቆየት መጣራቸውን ተናግረዋል። አሁንም የእርዳታ አቅርቦቱ በቂ አለመሆኑን፣ በብዙ አካባቢዎች ከመጠጥ ውሀ መጥፋት ጋር ተያይዞ የተቅማጥ በሽታ የመከሰት አዝማሚያ እየታየ ነው።
በሁሉም ክልሎች የሚገኙ ሹማምንት አፋጣኝ መፍትሄ ካልተገኘ የድርቁ ተጎጂ ቁጥር በእጥፍ ሊያድግ እንደሚችል ስጋት አላቸው።
በተያያዘ ዜና በም/ጠ/ሚ ደመቀ መኮንን የሚመራው የአደጋ መከላከል ግብረሀይል ትላንት ተሰብስቦ የተረጂው ቁጥር ወደ 10 ነጥብ 2 ሚሊየን ማደጉን ይፋ አድርጎአል። አያይዞም እስካሁን ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ የተገኘው
እርዳታ ከሚፈለገው አንድ ሶስተኛ ያህል ብቻ መሆኑን አረጋግጦአል። ይህ ሁኔታ በመንግስት አቅም ብቻ ችግሩን ለመቅረፍ እጅግ አዳጋች በመሆኑ መንግስት በቅርቡ የህዝቡን ድጋፍ ለመጠየቅ ይገደዳል ተብሎ ይጠበቃል።
አለም አቀፍ ማህበረሰቡ የተረጂው ቁጥር ከ15 ሚሊየን በላይ መሆኑን ቀደም ሲል ጀምሮ የገለጸ ቢሆንም መንግስት ቁጥሩን እርዳታ ለመለመን እንዲያመቻቸው ነው በማለት ሲያጣጥል ቆይቶ በሚቀጥሉት 2 ወራት የተረጅው ቁጥር ወደ 10 ሚሊየን ከፍ ይላል ብሎአል።

No comments:

Post a Comment