Wednesday, December 23, 2015

በኦሮሚያ ክልል በቦረና ዞን ህዝቡ ትግሉን አፋፍሞ ለመቀጠል እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ታወቀ ።

በደቡብ ኦሮሚያ ክልል በቦረና ዞን በሞያሌ ፣ ቡሌ ሆራ፣ ደሬ ፣ ያቤሎ ፣ ዱግደዳዋ ፣ ተልተሌ ፣ አሬሮና በሌሎችም ወረዳዎችና ቀበሌዎች የሚገኙ መምህራን ፣ ተማሪዎች፣ ገበሬዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ትግሉ የሚፈልገውን አስፈላጊውን መሰዋዕትነት በመክፈል እስከ መጨረሻው ለመጓዝ መቁረጣቸውንና እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ገለፁ ።

የኦሮሞ ህዝብ ሴት ወንዱ ወጣት አዛውንቱ ለነፃነቱ እየታገለ ባለበት ሁኔታ እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ከጨቋኞች ጎን እንደመቆም ይቆጠራል ያሉት ነዋሪዎቹ :
የኦሮሞ ህዝብ ታግሎና ደሙን አፍሶ በሚያመጣው ነፃነት አንገታችንን ቀና አድርገን መራመድን አንመኝም በማለት በመላው ሃገሪቱ የሚገኘው ማህበረሰባችን ከሚያደርገው እንቅስቃሴ ጎን ለጎን በመጓዝ ታሪክ ለመስራት መዘጋጀታቸውን ለሪፐርተራችን ገልፀዋል ።
የገዢው መንግስት ባለስልጣናት የህዝብን ቁጣ ለማብረድ በማሰብ ኀብረተሰቡን ጠርተው ለማነጋገር ሙከራ ቢያደርጉም : የወንዱን ፣ የሴቱን ፣ የወጣት ፣ አዛውንቱን ደም እያፈሰሳችሁ ከእናንተ ጋር የምናደርገው ምንም አይነት ስብሰባ የለም በማለት : ለአምባገነኖቹ እምቢተኝነቱን እያሳየ መሆኑንና በአካባቢው የሚገኙ መምህራን ተማሪዎች ከህብረተሰቡ ጋር እየተነጋገሩና ለቀጣዩ ትግል እራሳቸውን እያዘጋጁና እስትራቴጂ እየነደፉ መሆኑን ምንጮቻችን አያይዘው ጠቅሰዋል ።
የመንግስት ባለሰልጣናቱ አንዱ አካባቢ አልሳካ ሲላቸው ፣ ወደሌላው አካባቢ በመሄድና ስብሰባ በመጥራት ፣ ህብረተሰቡን ለማስፈራራት እየጣሩ ሲሆን የህዝቡን ጠንካራ አቋምና ወኔውን ሲመለከቱ ባለስልጣናቱ መደናገጣቸውን መርበድበዳቸውን ምንጮቻችን አያይዘው ገልፀዋል ።
እንደ ምንጮቻችን ዘገባ
በቦረና ዞን በተልተሌ ወረዳ ፣ በሆርባቴ ፣ በመርመሮ ፣ በዲቤ ገያ ፣ እና በሌሎች ቀበሌዎች የሚገኙ ነዋሪዎችም የተማሪዎቻችን ደም በከንቱ ፈሶ አይቀርም የተማሪዎቻችንን ደም ያፈሰሱትን እስከ መጨረሻው እንታገላቸዋል እንፋረዳቸዋለን ማለታቸውን እንዲሁም በያቤሎ ፣ በሞያሌና በሜጋና በአሬሮ ያሉ ተማሪዎችና ገበሬዎች ተቃውሞውን አጠናክረው ለመቀጠል ዝግጅታቸውን እንደጨረሱ መረጃዎች ደርሶናል ።
ባለፋት ሳምንታት በቦረና ዞን በሂዲ ዶላ ወረዳ የአንደኛ ደረጃና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሆ ብለው በመውጣት ማስተር ፕላኑን መቃወማቸው የሚታወስ ሲሆን የት/ ቤቱ አሰተዳደር አቶ ልደቱ ደረጄ የሚባል ግለሰብ ይህን እንቅስቃሴ የመራኸው አንተ ነህ በሚል ከስራው መታገዱ ምንጮቻችን ዘግበዋል።
ይህን የሂድ ዶላ እንቅስቃሴ ተከትሎም : በቦረና ውስጥ እየተቀጣጠለ ያለው እንቅስቃሴ መንግስትን ያስደነገጠ ሲሆን :
በአሁኑ ሰአት ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በዚህ ጨቋኝና አምባገነን ስርዓት የተማረረ በመሆኑ ይህን ስርአት ለመገርሰስ በቆራጥነትና በወኔ መነሳታቸውን ለምንጮቻችን ገልፀዋል
የአካባቢ ነዋሪዎች ለምንጮቻችን እንደገለፁት : ኦሮሚያ የተለያዩ ብሄር ብሔረሰቦች የሚኖሩባት ክልል መሆኗን ገልፀው ይህ እንቅስቃሴ የትኛውንም ብሄርና ማህበረሰብ የሚያሰጋ እንደልሆነና ምንም አይነት ፍርሀትና ስጋት ሊኖር እንደማይገባ አሳስበው
ጥያቄው መብትን የማስከበር ፣ ጥያቄና ሰላማዊ በመሆኑ ከህዝቡ ጎን በመቆም ትግሉን ሊቀላቀሉና ሊያግዙ ይገባል ብለዋል ።
በዚሁ በቦረና ዞን ቀደም ብሎ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች እንዲሁም የዱግደዳዋ ወረዳ ነዋሪዎች ማስተር ፕላኑን በመቃወም ከባድ ተቃውሞ ማድረጋቸው ይታወሳል ።
በስተመጨረሻ አምነስቲ ኢንተርናሽናል እና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች: መንግስት በዚህ ሰላማዊ እንቅስቃሴ ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃ አውግዘው የመንግስት ህገወጥ እርምጃ ህዝቡን ሰላማዊነቱን ጠብቆ እንዳይጓዝ እንዳያደርገው አሳስበዋል

No comments:

Post a Comment