Monday, December 7, 2015

በኦሮምያ የሚታየው ተቃውሞ እንደቀጠለ መሆኑን ከተለያዩ አካባቢዎች የሚደርሱን መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ኀዳር ፳፯ (ሃያ ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ባለፈው ሳምንት ፖሊሶች በወሰዱት እርምጃ ግቢያቸውን ጥለው ወጥተው የነበሩት የሁሌቦራ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች፣ ወደ ግቢያቸው ተመልሰው ከገቡ ቡዋላ እሁድ ለሰኞ አጥቢያ ሌሊቱን ተቃውሞ ሲያሰሙ አድረዋል። ዛሬ ጠዋት ፖሊሶች ወደ ግቢ በመግባት በተማሪዎች ላይ አስለቃሽ ጭስና ድብደባ በመፈጸማቸው በርካታ ተማሪዎች ተጎድተው ሆስፒታል ገብተዋል። ቲቲሲ ኮሌጅና የቴክኒክና ሙያ ተማሪዎችም እንዲሁ ዬዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ተቀላቅለው ተቃውሞ አሰምተዋል።የሁለተኛ እና የመሰናዶ ተማሪዎችም እንዲሁ ተቃውሞውን ተቀላቅለዋል። ፖሊሶች ሆስፒታሉን መክበባቸውን ተከትሎ ወላጆች እና ፖሊሶች የተጋጩ ሲሆን፣ ሁለት ፖሊሶች ተድብድበዋል። አንደኛው ፖሊስ በከፍተኛ ሁኔታ ተጎድቶ ህክምና እየተደረገለት ነው።ፖሊሶች በአንድ ቤት ውስጥ አስለቃሽ ጭስ በመተኮሳቸው፣ በቤቱ ውስጥ የነበሩ ህጻናት አየር አጥሮአቸው በመውደቃቸው ወዲያው ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል።

ተቃውሞውን ተከትሎ በሁሌቦራ ባንኮችን ጨምሮ ሁሉም የመንግስት መስሪያ ቤቶች እንዲዘጉ ታዟል። በዚሁ ዞን ዱገዳዋ ወረዳ ፍንችዋ ከተማ ላይም የሁለተኛና የመሰናዶ ተማሪዎችም ወደ መሀላኢ ከተማ በመሄድ ተቃውሞ እያሰሙ ነው። ወደ ገጠር አካባቢ ደግሞ አርጡሜ ለማ አንደኛ ደረጃ ትምርት ቤት፣ ቅሌሶ ረሳ ሁለተኛና መሰናዶ ትምህርት ቤት፣ ሩሰሃንቁ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተቃውሞ አሰምተዋል። በተማሪዎችም ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ተስምቷል።
በአዳማ ዩኒቨርስቲም ከጧቱ 2 ሰአት ጀምሮ ተቃውሞ የተነሳ ሲሆን፣ ፖሊሶች የሃኢል እርምጃ በመውሰድ ተቃውሞውን ለመቆጣጠር ሙከራ አድርገዋል።
በዲላ ዩኒቨርስቲም እንዲሁ ተመሳሳይ ተቃውሞ በዩንቨርስቲው ቅጥር ግቢ ውስጥ ተካሂዷል። ተማሪዎቹ ከግቢው እንዳይወጡ በከተማው ፓሊስ እና በልዩ ሀይል ታግተው ውለዋል። ፖሊሶች በግቢው ውስጥ በመግባት ተማሪዎችን ደብድበዋል።
በጅማ ዩኒቨርስቲ እሁድ ከምሽቱ 4 ሰአት ላይ ተቃውሞ የተነሳ ሲሆን፣ ፖሊሶች በአስለቃሽ ጭስ ተቃውሞን በትነውታል። ብዙ ተማሪዎችም አየር አጥሯቸው ሆስፒታል ተወስደዋል።
በሱሉልታም እንዲሁ ህዝቡ በብዛት ወጥቶ ተቃውሞ አሰምቷል። በምዕራብ ሸዋ ዞን በአደኣ በርጋ ወረዳም በሙገር እና በእንጭኒ ከተሞች ተቃውሞ ተደርጓል።ህዝቡ በአካባቢው የተሰማሩ ባለሃብቶች ለህዝቡ ምንም ጥቅም እየሰጡ አለመሆኑን ሲገልጹ፣የወረዳው አስተዳደር ፣የሃይማኖት አባቶች እና የአገሪቱ ሽማግሌዎች በመውጣት ህዝብን ለመምከር ሞክረዋል።
ደብረዘይትን ጨምሮ ተቃውሞ ሊነሳባቸው ይችላል በተባሉ ቦታዎች የመንግስት ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል።የአምቦ ዩኒቨርሲቲ የአዋሮ ካምፓስ ተማሪዎች እስራትና ድብደባው ሲበዛባቸው ግቢውን ለቀው ወጥተዋል።
በሆሮማያ ዩኒቨርስቲ የዩኒቨርስቲው ሴኔት ያወጣውን መግለጫ “ችግሩን የሚያባብስ ነው” በሚል መምህራን ተቃውመውታል። ሴኔቱ ተማሪዎች ሰኞ በትምህርት ገበታቸው ላይ እንዲገኙና ማክሰኞ ፈተና እንዲጀምሩ ያዘዘ ሲሆን፣ መምህራን በበኩላቸው ተማሪዎች ወደ ቤተሰቦቻቸው የሄዱ በመሆኑ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ዩኒቨርሰቲው ተመልሰው ፈተና ለመውሰድ እንደማይችሉ ተከራክረዋል።አብዛኞቹ ተማሪዎች አካባቢውን ለቀው ወደ ቤተሰቦቻቸው ሄደዋል።
ዛሬ ከሰአት በሁዋላ ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በተለያዩ አካባቢዎች እየተገደሉና እየተደበደቡ ያሉ የኦሮሞ ተማሪዎችን ለማስታወስ መሰባሰባቸውን ተከትሎ፣ ከአራት ኪሎ እስከ ስድስት ኪሎ ባለው መንገድ ላይ የፌደራል እና የአዲስ አበባ ፖሊሶች በብዛት ቆመው ታይተዋል። በተለይ ስድስት ኪሎ ግቢ አካባቢ ፖሊሶች በመኪኖች ላይ ሆነው ከግቢው ፊት ለፊት በመቆም ጥበቃ ሲያደርጉ ውለዋል። በተለያዩ የፖሊስ ካምፖችም፣ ፖሊሶች በተጠንቀቅ ቆመው ትእዛዝ እንዲጠባበቁ ተነግሯቸዋል።
የአሁኑ ተቃውሞ መንግስት የአዲስ አበባ ማስተር ፕላንን ተከትሎ የተደረገውን ተቃውሞ በቁጥጥር ስር ማዋሉን በተናገረ ማግስት የተደረገ ነው። ተቃውሞው በተወሰኑ የኦሮምያ አካባቢዎች እንደተካሄደ መንግስት ቢግልጽም፣ ተቃውሞው ግን በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች እየተካሄደ ነው።

No comments:

Post a Comment