Tuesday, December 29, 2015

የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ወጣቶቸ እያደኑ ማሰራቸውን ቀጥለዋል

ታኀሳስ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በኦሮምያ የተጀመረው ህዝባዊ አመጽ እንደገና ባገረሸበት ማግስት አመጹን ደግፈዋል በሚል በክልሎች እና በአዲስ አበባ የተለያዩ ወጣቶች እየተያዙ በመታሰር ላይ ናቸው። በአንቦና ወለጋ ዩኒቨርስቲዎች በርካታ ተማሪዎች ታሰሩ ሲሆን፣ በማህበራዊ ሚዲያው የተለያዩ ጽሁፎችን በመጻፍ ከሚታወቁት መካከል ደግሞ የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ወጣት ዮናታን ተስፋየ በደህንነት ሃይሎች ታፍኖ ማእከላዊ እስር ቤት ተወስዶ ታስሯል።
ዮናታን ባለፈው ግንቦት ተደርጎ በነበረው ምርጫ ሰማያዊውን በመወከል ባደረገው የምርጫ ክርክር ብዙዎች ድጋፋቸውን ሰጥተውት ነበር። ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ እየሩሳሌም ተስፋውና ፍቅረማርያም አስማማው ሰላማዊ ትግል ታጋዮችን ከማስበላት በስተቀር ለውጥ አያመጣም በሚል ሰማያዊ ፓርቲን ከለቀቁ በሁዋላ አርበኞች ግንቦት7ን ለመቀላቀል ሲሄዱ መንገድ ላይ መያዛቸውን የገለጹ ሲሆን፣ ጓደኛቸው ዮናታን ተስፋየ ግን በሰላማዊ ትግል ለውጥ ማምጣት ይቻላል በሚል በፓርቲው ውስጥ ታቅፎ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል። ወጣት ዮናታን፣ የኦሮሞ ወጣቶች ተቃውሞ ማንሳታቸው ተከትሎ በሚሰጣቸው አስተያየቶች ከገዢው ፓርቲ ካድሬዎች የተለያዩ ማስፈራሪያዎች ሲደርሱት ቆይቷል።
ከወጣት ዮናታን በፊት በማህበራዊ ሚዲያዎች የጎላ ተሳትፎ የነበረው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ተይዞ ታስሯል።
መንግስት ባለፉት ሶስት ሳምንታት ብቻ የኦፌኮ አመራር የሆኑትን እነ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ ከ5 ሺ በላይ የኦሮሞ ወጣቶችን አስሯል። ከ124 ያላነሱ ሰዎች ደግሞ በጸጥታ ሃይሎች ተገድለዋል።

No comments:

Post a Comment