Friday, December 18, 2015

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ተደብድበው ታሰሩ

ታኀሳስ ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ትናንት ምሽት የፌደራል ፖሊስ አባላት 6 ኪሎ ግቢ በመግባት 2 ተማሪዎችን ማሰራቸውን ተከትሎ የታሰሩት ተማሪዎች እንዲፈቱ በሰልፍ የጠየቁ ተማሪዎች በፖሊሶች ተደብድበዋል። ዩኒቨርስቲው ከጠዋት ጀምሮ በፖሊሶች ተከቦ ያረፈደ ሲሆን፣ ከቀኑ 7 ሰዓት ተኩል አካባቢ የፌደራል ፖሊሶች ወደ ግቢው በመግባት በርካታ ተማሪዎችን እየደበደቡ ወስደው አስረዋል። ከአራት ኪሎ ግቢ እስከ ስድስት ኪሎ ግቢ ባለው መንገድ በርካታ የፖሊስ አባላት ቅኝት ሲያደርጉ አርፍደዋል። እስካሁን በደረሰን መረጃ ከ50 በላይ ወጣቶች ሲታሰሩ ፣ ፌደራል ፖሊስ ተማሪዎቹን ማደሪያ ክፍላቸው እየገቡ ደብድቧቸዋል።

በሰሜን አዲስ አበባ ውጥረት ሰፍኖ መዋሉንም ዘጋቢዎቻችን ገልጸዋል።
መንግስት ስልጣኑን ለማስጠበቅ የተለያዩ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ሲሆን፣ በርካታ የመከላከያ አባላት በምሽት ወደ አዲስ አበባ ገብተዋል። ይሁን እንጅ ለሱዳን የሚሰጠውን መሬት ተከትሎ በሰሜን ተቃውሞ ሊነሳ ይችላል በሚል ተጨማሪ ሃይል ወደ ሰሜን መላኩም ታውቋል።
የገዢው ፓርቲ የጸጥታ ሃይሎች በንጹሃን ዜጎች ላይ የሚወስዱት እርምጃ አስከፊ መሆኑንም በየቦታው የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በጫንቃ ልጃቸውን ለመከላከል የሞከሩ እናት ከተገደሉ በሁዋላ ፣ ወረፋ ጠብቁ ብለው የተናገረች ነርስና የሆስፒታሉ ጠባቂ በተመሳሳይ መልኩ ተረሽነዋል። በነጆ የነበረውን ተቃውሞ ተከትሎ 5 ታማሪዎች ተገድለውና በርካታ ተማሪዎች ቆስለው ሆስፒታል ከገቡ በሁዋላ የመጡ ቁስለኛ የፌደራል ፖሊስ አባላት ቅድሚያ እንዲሰጣቸው ጠይቀው ፣ ሃኪሞቹ ግን ልዩነት ሳያደርጉ ሁሉንም እንዳመጣጡ እንደሚያስተናግዱ በመናገራቸው የተበሳጨ አንድ የፌደራል ፖሊስ የፈጥኖ ደራሽ አባል ” የሆስፒታሉን ነርስና የጥበቃ ሰራተኛውን “ገድሏል። የሁለቱም ሟቾች የቀብር ስነስርዓት ከአምስቱ ተማሪዎች ጋር በአንደነት ተፈጽሟል።
ትናንት በሙገር ከተማ በተደረገው ህዝባዊ ተቃውሞ ቢያንስ 10 ሰዎች ተገድለዋል። እስካሁን ድረስ ባለው መረጃ ከ100 ያላነሱ ሰዎች በወታደሮች ተገድለዋል። ግድያውን የአሜሪካ ኢምባሲ አሳሳቢ ነው ብሎታል።
መንግስት በህዝቡ ላይ የሚወስደውን ጥቃት እንዲያቆምና ተቃውሞው የሚበርድበትን አፋጣኝ መፍትሄ እንዲፈልግ በተባባሩት መንግስታት ድርጅት የአሜሪካ አምባሳደር የሆኑት ሳማንታ ፓወር በቲውተር መልእክት አስተላልፈዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ዳሳለኝ ንግግር ተጨማሪ ደም መፋሰስ የሚያስከትል ነው በማለት ስጋታቸውን ገልጸዋል። ፖሊሶች በሱሉልታ፣ በቡራዩ፣ በባሌ ሮቤ እና በሌሎችም የኦሮምያ ከተሞች በመዘዋወር በብስጭት የሳተላይት ዲሾችን መንቀላቸውንም የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በባሌ ሮቤ በተለይ ዶንሳና ኪብጠቴ በሚባሉ ሰፈሮች ብዙ ዲሾች ተሰባብረዋል፣ ህዝቡም ዲሾቹን እየነቀለ ወደ ቤቱ እያስገባ ነው።
በሱሉልታ፣ ሰንዳፋና ወሊሶ የታጠቁ የመንግስት ሃይሎች የአማራን ቤቶችና ንብረት በማውደም ሁለቱን ብሄሮች ለማጋጨት ከፍተኛ ስራ እየሰሩ መሆኑን ነዋሪዎች ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment