Sunday, January 3, 2016

በቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያና በሕዝቧ ላይ እየደረሰ ስላለው ሁኔታ ከለንደን ደብረጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

በአሁኑ ወቅት በቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያና በሕዝቧ ላይ እየደረሰ ስላለው ሁኔታ ከለንደን ደብረጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ መግለጫ።

“ጻድቃን ጮኹ፤ እግዚአብሔርም ሰማቸው፤ ከመከራቸውም ሁሉ አዳናቸው።” (መዝ፡ 34፡ 17)
ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ ፈጣሪን በማወቅና የክርስትና ሃይማኖትን በመቀበል ቀደምት ከተባሉት የዓለም ሀገራት አንዷ ስትሆን ሕዝቧም በፈሪሃ እግዚአብሔር የታነፀ፤ ጨዋ ኩሩ እና ዘር ሃይማኖትና ቋንቋ ሳይከፋፍለው በመቻቻል፤ በመፈቃቀርና በመከባበር በሰላም አብሮ መልካም ምሳሌ ሆኖ የኖረ ነው።
ይህ ሃገር ወዳድ፤ ሃይማኖተኛና ጀግና ታላቅ ሕዝብ ለሃገሩ ለሃይማኖቱና ለነፃነቱ ባለው ቀናዒነት በየጊዜው የሃገሩን ዳር ድንበር በመድፈር፤ ነፃነቱን ለመግፈፍና ሃይማኖቱን ለማጥፋት የተነሱበትን ጠላቶች በጋራ ክንዱ በመመከት የሃገሩን ድንበርና ሉዓላዊነት በደምና በአጥንቱ ጠብቆ ነፃነቱን አስከብሮ በመኖር ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ መኩሪያ የሆነ ነበር።
ከቅርብ ዓመታት ጀመሮ ግን በዚህ ታላቅ ሕዝብ መካከል ሰውን በዘር፤ በቋንቋ እና በሃይማኖት የሚከፋፍልና የሚያቃርን ክፉ መንፈስ ሆነ ተብሎ እየተረጨበት፤ ይኸው ክፉ መንፈስ በአንዳንድ አካባቢ ኗሪዎች መካከል ጥርጣሬና መጠላላትን ፈጥሮ ወደ እርስ በእርስ ግጭት በመሸጋገር በዚህ ግጭት ሳቢያም በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰ ይገኛል።
ይህን የመሰለ ሕዝብን በሕዝብ ላይ የማነሳሳትና የመከፋፈል ተግባር በእንጭጩ ካልተገታና ካልቆመ ደግሞ በአጠቃላይ የሀገር አንድነትና ህልውና ላይ አደጋን ሊያስከትል የሚችል ሁኔታን እንደሚፈጥር መገመት አዳጋች አይሆንም።
ከዚሁ የእርስ በእርስ ግጭት ውስጥም በተለይ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ፡
1ኛ) በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በጎንደርና አካባቢው የቅማንትና የአማራ ጎሳ በሚል ከፋፋይ ሴራ ምክንያት በተነሳ የእርስ በእርስ ጦርነት በሰው ህይወት ላይ የደረሰው ጉዳት አንዱ ሲሆን በዛው በጎንደር አካባቢ በሚገኝ በሺህ የሚቆጠር ታሳሪ ባለበት እስር ቤት ውስጥ በተነሳ የእሳት ቃጠሎ ሳቢያ ከእሳቱ ለማምለጥ በሞከሩ እስረኞች ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተኩስ በመክፈት በፈጸሙት እግዚአብሔር የማይወደው የጭካኔ ተግባር ጭምር አያሌ ሰላማዊ ሰዎችም እንዲሁ ህይወታቸው ሊያልፍ ችሏል።
2ኛ) በደቡብ፤ በምሥራቅና በምእራብ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በኦሮሞ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ተጀምሮ በሕዝቡ ውስጥ የተስፋፋው ሰላማዊ የመብት ጥያቄን ተከትሎ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች በወሰዱት ሰብዓዊነት የጎደለው እርምጃ፤ ባልታጠቁ ሰላማዊ ሰዎች ላይ ተኩስ በመክፈት በመቶ የሚቆጠሩ ወንዶች፤ ሴቶች፤ እናቶች፤ አባቶች፤ ህፃናትና ነፍሰ ጡር ሳይቀሩ በጭካኔ ተገድለዋል፤ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ደግሞ ለእስርና ለእንግልት ተዳርገው ይገኛሉ።
3ኛ) ከዚህ በተጨማሪ የወቅቱ የኢትዮጵያው አገዛዝ መንግሥት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በጎንደርና በሱዳን አዋሳኝ የሚገኝ እጅግ ሰፊና ለም የኢትዮጵያ መሬት ለሱዳን መንግሥት አሳልፎ ሊሰጥ መዋዋሉን በማስመልከት የአካባቢውን ኗሪዎችም ሆነ መላ ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያንን ከማስቆጣቱና ከማስነሳቱም በላይ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ሁኔታ የአካባቢው አርሶ አደሮችን ከመኖሪያችው ከማፈናቀሉ አልፎ በዚሁ ሳቢያ ከውስጥና ከውጪ በሚነሱ የአካባቢው ግጭቶች በሰላማዊ አርሶ አደሮችና ኗሪዎች ላይ ከፍተኛ የህይወት አደጋ እየደረሰ ይገኛል።
ይህ ሁኔታ በዚሁ መልክ ከቀጠለ ደግሞ በሃገራችን ላይ ሌላ ዙር ጦርነትና ብጥብጥን በመጫር በሰውም ሆነ በንብረትና ከዛም አልፎ በሃገር ህልውና ላይ አደጋ እንዳያስከትል እየተሰጋ ይገኛል።
4ኛ) ከሁሉም በላይ የሚያሳዝነው፤ የሚያስቆጨውና እግዚኦታ የሚያስፈልገው ደግሞ ይህንን የመሰለ እግዚአብሔር የማይወደውና ሰብዕና የጎደለው ድርጊት በዛ ሕዝብ ላይ የሚፈጸመው ከአሥር ነጥብ አምስት ሚሊዮን በላይ የሚሆነው የሀገሪቱ ሕዝብ የሚላስና የሚቀመስ አጥቶ ለከፍተኛ ረሃብና እርዛት በመዳረግ የሞት ጥላ አጥሎበት በሚገኝበት ወቅት መሆኑ ነው።
ይህ ከላይ በአጭሩ የተገለጸውና ሌሎች በሃገራችን ኢትዮጵያና በሕዝቧ ላይ የሚደርስን ማንኛቸውንም ሕዝብን ከሕዝብ ከፋፋይ የሆነ ተግባርን፤ የሰብዓዊ መብት ጥሰትን፤ ግድያ፤ ፍትሐዊ ያልሆነ እግዚአብሔር በአምሳሉ የፈጠረው ሰብዓዊ ፍጡርን እስራትና መንገላታትን ሁሉ ርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደ ቤተ ክርስቲያን በጽኑ ታወግዛለች።
ለሀገሩና ለሃይማኖቱ ቀናዒ፤ ነፃነቱንና ክብሩን ጠባቂ የሆነው ታጋሽና አርቆ አስተዋይ የኢትዮጵያ ሕዝብም ነጻነት፤ ከብርና ፍትሕን እንጂ ኢ ፍትሐዊ በሆነ በመሪር አገዛዝና በጽኑ የአገዛዝ ቀንበር ሥር እንዲውል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልትፈቅድና ድርጊቱንም በዝምታ ልታልፍ የሚገባት አይሆንም።
ይህም በመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሁሌም በመሪር የአገዛዝ ሥር ቀንበር ሥር ለሚገኙና በጽኑ የአገዛዝ ጭቆና ሥር ስለወደቁ ሕዝቦች ፈጣሪ ይራዳቸው ዘንድ ጸሎት ማካሄዷን ሳታቋርጥ ትቀጥላለች።
በዚህ መሠረት የርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ባለፉት ሳምንታትም ሆነ እስከ አሁንም ድረስ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በተደረጉ እንቅስቃሴዎች ህይወታቸው ለጠፋ የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ ጥልቅ ሃዘኗን እየገለጸች ለሟች ቤተ ሰቦች መጽናናትንና ጥንካሬን እንዲሁም የሞቱትን ደግሞ እግዚአብሔር ነፍሳቸውን ከጻድቃን ሰማዕታት ጎን በሰላም ያሳርፍ ዘንድ ለፈጣሪ ጸሎቷን ታቀርባለች።
በመጨረሻም በሃገራችን ኢትዮጵያና በሕዝቧ ላይ ፍትሕ ሲዛባ፤ ሰብዓዊ መብት ሲጣስና ሃገርን፤ ሕዝብንና ሃይማኖታችንን ለአደጋ የሚያጋልጥ ሁኔታ ስፈጠር ርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ሁሌም እንደምታደርገው እንደ ቤተ ክርስቲያን ለሀገር፤ ለሕዝብና በመወገን በጸሎትም፤ ሆነ በአቋም መግለጫ ድምጿን ከፍ አድርጋ በመጮህ ሁኔታውን ለኢትዮጵያና ለዓለም ሁሉ ማሰማቷን ሳታቋርጥ ትቀጥላለች።
“ኃጢአተኞችን ክፋት ይገድላቸዋል ጻድቃንንም የሚጠሉ ይጸጸታሉ።” (መዝ፡ 34፤ 21)
ልዑል እግዚአብሔር ለውድ ሀገራችን ሰላምን፤ ለሕዝባችንም አንድነትን ይስጥልን!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! አሜን!!

No comments:

Post a Comment