Wednesday, January 13, 2016

የአውሮፓ ህብረት በኦሮሚያ ክልል እየተካሄደው ስላለው ተቃውሞ ከዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ማብራሪያ ጠየቀ

ኢሳት (ጥር 4 ፥ 2008)
የኢትዮጵያ ዋነኛ የልማት አጋር የሆነው የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በህብረቱ ዋና መቀመጫ ብራሰልስ ከተማ ተገኘተው በኦሮሚያ ክልል እየተካሄደ ስላለው ተቃውሞ ማብራሪያን እንዲሰጡ ጠየቀ። ሆኖም የተዘጋጀላቸውም ጋዜጣዊ መግለጫ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ተሰርዟል።
የቀረበላቸውን ጥያቄ ተከትሎ በብራሰልስ የሚገኙት ዶ/ር ቴዎድሮስ በጉዳዩ ዙሪያ ከህብረቱ አባል ሃገራት በርካታ ጥያቄዎች ይቀርብላቸዋል ተብሎ በመጠበቅ ላይ መሆኑን መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
በኢትዮጵያ የኦሮሚያ ክልል ኣየተካሄደ ያለው ተቃውሞ ስጋት እንደደረሰበት የገለጸው ህብረቱ፣ የጸጥታ ሃይሎች እየወሰዱ ያለው እርምጃ በአስቸኳይ እንዲቆም አሳስቧል።
መቀመጫቸውን በአውሮፓ ያደረጉ በርካታ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በበኩላቸው ህብረቱ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጠንካራ መልዕክት እንዲያስተላልፍ ዘመቻ መክፈታቸውም ታውቋል።
በሂውማን ራይትስ ዎች የአውሮፓ ህብረት ተወካይ የሆኑት ሎቲ ሌችት ህብረቱ ዝምታውን በመስበር የኢትዮጵያ መንግስት እየወሰደ ያለውን የሃይል እርምጃ ማውገዝ እንደሚገባው ገልጸዋል።
የአውሮፓ ህብረም የልማት ድጋፍ በሚያደርግላት ኢትዮጵያ ለተቃውሞ አደባባይ በወጡ ሰዎች ላይ የጥይት ምላሽ ሳይሆን ነገሮችን በድርድር እንዲፈቱ ግፊቱን ማጠናከር ይኖርበታል ሲሉ ተወካዩ አልክለው አስታውቀዋል።
በአውሮፓ ማብራሪያ ለመስጠት የሚገኙ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በኦሮሚያ ክልል ስላለው ተቃውሞ ከሚሰጡት ማብራሪያ በተጨማሪ በሃገሪቱ እየተባባሰ ስላለው የድርቅ አደጋም ዝርዝር መረጃን ይሰጣሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን የተገኙ መረጃዎች አመልክተዋል።
ይኸው በኦሮሚያ ክልል ዳግም ተቀስቅሶ የሚገኘው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ተቃውሞ ትኩረት ስቦ የሚገኝ ሲሆን በርካታ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች የጸጥታ ሃይሎች እየወሰዱ ባለው እርምጃ የሟቾች ቁጥር እያሻቀበ መሆኑን አመልክተዋል።
ለኢትዮጵያ መንግስት የልማት ድጋፍን የሚያደርጉ ሃገራትም በሃገሪቱ ያለው ተቃውሞና የሰዎች ሞት አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን በመረዳት መንግስት በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ እንዲሰጥ ማድረጋቸውንም ለመረዳት ተችሏል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአውሮፓ ህብረት ጥሪ በቤልጂየም ብራሰልስ የሚገኙ ዶ/ር ቴዎድሮስ ሲሰጡት የነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰርዟል። ጋዜጣዊ መግለጫ የተሰረዘበት ምክንያት የታወቀ ነገር የለም።

No comments:

Post a Comment