Friday, January 22, 2016

በኦሮምያና በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተፈጸሙ ወንጀሎችን የሚያወግዙ የተቃውሞ ሰልፎች ተደረጉ

ጥር ፲፫ (አሥራ ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ጥር 13 ቀን 2008 ዓም በአውስትራልያ ብሪዝቤን ከተማ የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ በአይነቱ ልዩ የተባለለት ነው። ህብረ ብሄራዊነት በተንጸባረቀበት በዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ተሳታፊዎቹ በጋራ የኢትዮጵያን መንግስት ያወገዙ ሲሆን፣ በተለይም ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ በዜጎች ላይ እየፈጸመ ያለውን ግድያ ማፈናቀልና እስራት፤ በጎንደር ገበሬዎችን በማፈናቀል ለሱዳን መሬት ቆርሶ ለመስጠት እያደረገ ያለውን ታሪካዊ ክህደትና በኢትዮጵያ ኦጋዴን ተወላጆች ላይ እየፈጸመ ያለውን ጭፍጨፋ በጋራ አውግዘዋል።
ከብሪዝቤን ኩዊንስ ፓርክ የተነሳው ሰልፍ እልህና ቁጣ የተቀላቀለበት መፈክር በማሰማት ወደ ኩዊንስላንድ ፓርላማ መቀመጫ ቦታ አምርቷል።በፓርላማው ፊት ለፊት በመሰባሰብ ድምጻቸውን በማሰማት ላይ የነበሩትን ሰልፈኞች ለማናገር ሁለት የመንግስት ተወካዮች የተገኙ ሲሆን፣ ሰልፈኞቹም በተወካዮቻቸው አማካኝነት መልዕክታቸውን አቅርበዋል። በኩዊንስላንድ የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ማህበር፤ በኩዊንስላንድ የኦሮሞ ማህበረሰብ ማህበርና በኩዊንስላንድ የኦጋዴን ማህበረሰብ ማህበር ተወካዮች በየተራ የኢትዮጵያ መንግስት በዜጎቹ ላይ እየፈጸመ ያለውን ኢ ሰብአዊ ድርጊቶችን በዝርዝር አቅርበው። አውስትራልያ ያሏትን እድሎች ተጠቅማ ጫና መፍጠር እንድትችል ተመጽኗቸውን አሰምተዋል።
በጽሁፍ ያዘጋጁትን ደብዳቤ በስፍራው ተገኝተው ለነበሩት በግዛቷ መንግስት ተወካዮች በማስረከብ የሰልፉ ፍጻሜ ሆኗል።
በኩዊንስላንድ የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ማህበር፤ የኦሮሞ ማህበረሰብ ማህበርና የኦጋዴ ማህበረሰብ ማህበር በጋራ ባዘጋጁት የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች የተውጣጡ ተሳታፊዎች በጋራ በመቆም ለወገኖቻቸው ድምጻቸውን አስምተዋል። በተለይም ላለፉት 25 ዓመታት በህወሃት መራሹ መንግስ ሲሰራበት የነበረው የመለያየትና አንዱ ሌላውን በጥላቻ እንዲያይ የተሞከረበት አካሄድ መክሸፉ በገሃድ የታየበት መድረክ ነበር ስትል ኤልሳቤጥ ግዛው ሪፖርቷን አጠቃላለች።
ተመሳሳይ የተቃውሞ ሰልፍም በስውዲን ስቶክሆልም ተካሄዷል። ኢትዮጵያውያን በጋራ በመሰባሰብ ገዢው ፓርቲ በኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈጽመውን የመብት ጥሰት አውግዘዋል።
ከሰልፉ አስተባባሪዎች አንዱ የሆነው ጫላ ኦቦራ ፣ “ሰላማዊ ሰልፉ መንግስት በህዝቡ ላይ የሚፈጽመውን የመብት ጥሰት ከማጋለጥና ለህዝቡ ያለንን አጋርነት ከመግለጽ በተጨማሪ፣ ለስርዓቱ እኛ ከዚህ በሁዋላ ተከፋፍለን አንተን አንቃወምም በአንደነት ተባብረን ልንፈነግልህ ተዘጋጅተናል የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ነው ብሎአል
ሌላው በሰልፉ ላይ የተሳተፈው ጫላ ሃይሉ በበኩሉ ” በህዝባችን ላይ የሚፈጽመው ሁሉ ያመናል” ያለ ሲሆን፣ ህዝቡ በአንድነት ትብብር አድርጎ በቃን ማለት መጀመሩን ገልጿል።
ሌላው የሰልፉ አስተባባሪ አቶ ዘለሌ ጸጋ ስላሴ ሰላማዊሰልፉን በስዊድን የሚገኙ የተለያዩ የሲቪክ ድርጅቶች በጋራ ያዘጋጁት መሆኑን ገልጸው፣ በጣም የተሳካ ሰልፍ ነበር ይላሉ።

No comments:

Post a Comment