Saturday, January 30, 2016

የህዝባችን እንባ ለማቆም ሁላችንም አምርረን እንታገል

ኢትዮጵያ አገራችን ከፍተኛ የሆነ የህልውና ስጋት ተደቅኖባታል። ልጆቿ በያቅጣጫው ዋይታቸውን እያሰሙ ነው። የወያኔ የተበላሸ ስርዓት እና የስግብግብነት ተፈጥሮ ተደማምረው ህዝባችንን በቃላት ሊገለጽ በማይቻል ሰቆቃ ውስጥ ከተውታል። ህሊና ይዘው መፈጠራቸው ጥያቄ ውስጥ እስከሚገባ ድረስ፣ ቅልብ የወያኔ ገዳይ ወታደሮች በኦሮሞ እናቶችና ህጻናት ላይ የፈጸሙት ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ በረጅሙ ታሪካችን ያላየነውና ያልሰማነው ነው። ባለፉት መንግስታት ለነጻነታቸው የጮሁ ወጣቶች በስርዓቱ የጸጥታ ሃይሎች መገደላቸው ታሪክ የመዘገበው ሃቅ ነው፣ ነገር ግን ህጻናትና ታዳጊዎች እጅግ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ ግንባራቸውንና ደረታቸውን በጥይት እየተመቱ ሲወድቁ ስንመለከት ይህ በታሪካችን የመጀመሪያ ነው። አለም በፍጥነት እየተለወጠ ባለበት በዚህ ዘመን እንዲህ አይነት ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ መወሰዱ ደግሞ የአገዛዙ ቁንጮዎችንና እነሱን ተከትለው ወደ ጥፋት አረንቋ የሚተሙትን ሁሉ ከሰው መፈጠራቸውን እንድንጠይቅ የሚያደርግ ነው። የኦሮሞ ህዝብ በአጋዚ ወታደሮችና በፌደራል ፖሊሶች በግፍ ለተነጠቀው ልጆቹ ድምጹን ከፍ አድርጎ አልቅሷል፤ ቁጭቱን በቻለው መንገድ ሁሉ ሊገልጸው ሞክሯል። ነገር ግን እስካሁኗ ሰአት ድረስ መገደሉ፣ መታሰሩ፣ መሰደዱ፣ መዋረዱ አለቆመም። አገዛዙ ለአንድ ቀን በስልጣን ላይ ውሎ እስካደረ ድረስ ይኸው ግፍ ይቀጥላል።
የወልቃይት ህዝብ እኛ እንደፈለግን እንጅ አንተ እንደፈለክ አትኖርም ተብሎ ተፈርዶበት ያለፉትን 25 ዓመታት በስቃይ አሳልፏል። አሁንም እንደገና ” እኛ እናውቅልሃለን እየተባለ” መከራውን እየበላ ነው። በአካባቢው ያንዣበበው የሞት ደመና እጅግ አደገኛ ነው። እየተረጨ ያለው መርዝ ካልቆመ፣ አካባቢው በአጭር ጊዜ የግጭት አውድማ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው። ዘራፊው የህወሃት ቡድን ግጭትን ከማባበስ በተረፈ ችግሩን የማስቆም ፍላጎት አላሳዬም።

በዚሁ አካባቢ የአንድ አገር ሎጆችን ቅማንትና አማራ እያሉ እርስ በርስ ለመከፋፈልና ለማጋጨት ወያኔ እየዘራው ያለው ይጥፋት ዘር እስካሁን ከደረሰው እልቂት በላይ ሌላ እልቂት ይዞ እየመጣ ነው። የአገር ሰላምና ጸጥታ እናስከብራለን ብለው መሳሪያ የታጠቁ ሃይሎች በሁለቱም ወገን ግጭት ለመቀስቀስ ሲዶልቱ፣ ሲያቅራሩና ሲሸልሉ ውለው እያደሩ ነው። ከዚህ ሁሉ የእልቂት ጀርባ ያሉት ዜጎችን ካላጋጩ ውለው ማደር የማይችሉት የወያኔ መሪዎችና ግብረአበሮቹ ናቸው።
የደቡብ ህዝብም ልጆቹን በሞት እየተነጠቀ ነው። በሺዎች የሚቆጠሩ ልጆቹም በየእስር ቤቱ ታጉረዋል፡፡ ዛሬ ወደ ኮንሶ፣ አርባምንጭ፣ ቁጫ፣ ሃመር ወዘተ ብንሄድ የምንሰማው ዋይታና ለቅሶ ነው።
የሶማሌው ወገናችን በልዩ ሃይል አባላት የዘረ ፍጅት እየተፈጸመበት ነው፤ አፋሩ ፣ ጋምቤላውና ቤንሻንጉሉ ከቀየው እየተፈናቀለ፣ መሬቱን እየተነጠቀ ለሞትና ለዘላለማዊ ድህነት ተዳርጓል።
ይሄ ሁሉ መከራና ግፍ ሳያንስ ከ20 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው ህዝባችን በረሃብ እየተጠቃ መሆኑ በሰፊው እየተነገረ ነው። በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍል በተፈጥሮ በሚሳበብ የአየር መዛባት ችግር ምክንያት ባለፈው የምርት ዘመን የተዘራው ሰብል እንዳለ ወድሞአል:: በዚህም የተነሳ በህዝባችን ላይ ያንዣበበው የረሃብ አደጋ እስከዛሬ ካየነው ሁሉ የከፋ እንደሚሆን አለማቀፍ ድርጅቶች እያስጠነቀቁ ነው። ላለፉት 10 አመታት በእጥፍ አሃዝ የኢኮኖሚ እድገት አስመዝግቤያለሁ እያለ ህዝብ ሲያደነቁርና የለጋሽ አገሮችን ቀልብ ለመሳብ ሲባዝን የኖረው ወያኔ ግን በፈጠራ ታሪክ የገነባው ገጽታ እንዳይበላሽበት ረሀቡን ለመደበቅና የጉዳት መጠኑን ለማሳነስ ብዙ ርቀት ተጉዟል። ያም ሆኖ የችግሩ ግዝፈት እያየለ ሲመጣና ተጎጂዎች ከቀያቸው ተፈናቅለው ወደየ አጎራባች ከተሞች መሸሽ ሲጀምሩ ሳይወድ በግድ ለማመን ተገዷል። ። በሰሜን ወሎ፣ በትግራይ፣ በአማራ፣ በአፋር፣ በደቡብና በኦሮምያ በድርቁ ምክንያት በምግብ እጥረት እየተሰቃዩ የሚገኙ እናቶችና ህጻናት ቁጥራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ቢመጣም፣ ወያኔ ግን እንደ ኢኮኖሚው ሁሉ እዚህም ላይ የቁጥር ጨዋታ በመያዙ አሁንም ተገቢው እርዳታ ለህዝባችን በጊዜ እንዳይደርስ እየተከላከለ ለህዝብ መከራ ደንትቢስነቱንና ጨካኝነቱን እያሳየ ይገኛል።
ወያኔ በህዝባችን ላይ የደገሰው የሞት ድግስ በዚህ ብቻ አያበቃም። የኑሮ ውድነቱ ጣሪያ በመንካቱ ህዝቡ እያንዳንዷን ቀን የሚያሳልፈው በጣርና በጭንቅ ነው፤ ከጥቂት የወያኔ ባለስልጣናትና ሸሪኮቻቸው ውጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ኑሮው ሲኦል ሆኖበታል። ችግሩና መከራው እየከፋ ሲሄድ እንጅ እየቀነሰ ሲሄድ አይታይም። በሚብለጨለጩና የህዝቡን መሰረታዊ የፍጆታ ችግር በማይቀርፉ ስራዎች ላይ በማትኮር ህዝብን በልማት ስም ለመሸንገል ሙከራ ቢደረግም፣ አልተሳካም። ከኑሮ ውድነት በተጨማሪ ስራ አጥነቱ፣ አፈናው ፣ ስደቱ እስርና እንግልቱ፤ ሙስናው፣ የፍትህ እጦቱ ወዘተ የአገራችን ህዝብ ኑሮውን በጉስቁል እንዲገፋ አድርጎታል።

አርበኞች ግንቦት 7 አገራችንና ህዝባችን ከዚህ ሁሉ መከራና ስቃይ መውጣት የሚችለው አገዛዙ የዘረጋው የተበላሸ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ፖሊሲዎች ሲለወጡና ከህዝብ፡በህዝብ ለህዝብ የሚቆም የመንግሥት ሥርዓት በአገራችን እውን መሆን ሲችል ብቻ ነው ብሎ ያምናል:: የወያኔ የሥልጣን ዕድሜ በተራዘመ ቁጥር በህዝባችን ላይ የሚደርሰው በደልና ሰቆቃም እንዲሁ እየተራዘመ ይሄዳል:: ህዝባችን ከሚደርስበት ለቅሶና መከራ እንዲገላገል ሁላችንም በያለንበት አምርረን እንታገል::

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ
አርበኞች ግንቦት7

No comments:

Post a Comment