Tuesday, January 19, 2016

በሶማሊያ በአሸባሪዎች የተገደሉት የኬኒያ ወታደሮች አስከሬን በክብር ወደ አገሩ ተመለሰ

ጥር ፲ (አሥር) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ሕብረት ጦር አሜሶን ስር በመሆን በሶማሊያ ሰላም ለማስከበር ተሰማርተው የነበሩ የኬንያ ወታደሮች ባለፈው ሳምንት በአሸባሪዎች በተሰነዘረ ጥቃት መገደላቸውን ተከትሎ አስከሬናቸው ናይሮቢ ደርሷል።
የኬኒያ መከላከያ ሚንስትር የሆኑት ራቼሎ ኦማሞ ”በጣም ወሳኝ ዜጎቻችን! የወደቁ ጀግኖቻችን” ሲሉ ሟቾቹን አሞካሽተዋል።መንግስት የሟች ወታደሮችን ስም ዝርዝር ለቤተሰቦቻቸው አስታውቋል። ካሳም መክፍሉ ታውቋል።
የአፍሪካ ሕብረት ጦር አሜሶንን በገንዘብና በትጥቅ ከሚያግዙት በቀዳሚነት ተርታ የሚሰለፈው የአውሮፓ ሕብረት በበኩሉ ጥቃቱን አውግዞ በሶማሊያ ዘላቂ ሰላምንና መረጋጋትን ለማስፈን ይቻል ዘንድ ከትጥቅ ትግል ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሔት ሊበጅለት ይገባል ብሏል።
በሶማሊያ ሰላም ለማስከበር ከተሰማሩት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት ውስጥ ምን ያህሉ ሕይወታቸውን እንዳጡና የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው እስካሁን በግልፅ አይታወቅም። በተጨማሪም የሟች ቤተሰቦችና የኢትዮጵያዊያ ሕዝብ አሃዙን በውል ካለማወቁ በተጨማሪ አገራቸውን ወክለው ሰላም ለማስከበር ሲሉ የሞቱ የሰራዊቱ አባላት ብሄራዊ አቀባበል ሲደረግላቸው ታይቶ አይታወቅም። የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስቴር ሟቹ መለስ ዜናዊ መንግስት የሟች ወታደሮችን ቁጥር ለፓርላማ አባላት የማሳወቅ ግዴታ የለብንም ሲሉ መናገራቸው የሚታወስ ነው።

No comments:

Post a Comment