Tuesday, January 5, 2016

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ ያለው ርሃብ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን አሳወቀ

ታኀሳስ ፳፮ (ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የዓለም የምግብ ድርጅት በኢትዮጵያ ያለው የድርቅ ሁኔታ እየከፋ መምጣቱንና ዜጎች አፋጣኝ እርዳታ ካልተደረገላቸው በአገሪቱ የሚደርሰው ሰብዓዊ ቀውስ እጅግ አደገኛ መሆኑን በሪፖርቱ ገልጿል።
በኢትዮጵያ በተከሰተው የአየር መዛባት ኤሊኖ ምክንያት ወቅቱን ጠብቆ ዝናብ ባለመዝነቡ በቂ ምርት መሰብሰብ ያልተቻለ ሲሆን እንስሳትም በድርቁ ሰበብ ሞተዋል።
ቁጥራቸው ከ10 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያዊያን አፋጣኝ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ሲሆን የዓለም የምግብ ድርጅት 7.6 ሚሊዮን የሚሆኑትን በ2016 ዓ.ም ለመርዳት መዘጋጀቱንና ባለፉት ስድስት ወራቶች ውስጥ ከ5% ያነሰ የምግብ አቅርቦት ግብዓቶችን ማድረሱን የድርጅቱ ቃል አቀባይ እስቴፋን ጁሪክ አስታውቀዋል።
በኢትዮጵያ የተከሰተው ድርቅ ባለፉት ሰላሳ ዓመታት ተከስተው ከነበሩት ሁሉ የከፋውን ቀውስ ያስከተለ መሆኑን የተባባሩት መንግስታት ድርጅት በሪፖርቱ ማሳሰቡን ዩኤን ኒውስ ዘግቧል።
በተጨማሪም በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይና አማራ ክልል፣ በምስራቅ ኦሮሚያና ሶማሊያ ድርቁ ባስከተለው ችግር ሕጻናት በተመጣጠነ የምግብ እጥረት ምክንያት ለሞት መጋለጣቸውንና በአገሪቱ ያለው የርሃብ ተጠቂዎች ቁጥር 20 ሚሊዮን እንደሚጠጋ የካቶሊክ የእርዳታ ድርጅትን ጠቅሶ አልጀዚራ ዘግቧል። ከየአካባቢው በተሰባሰቡ መረጃዎች መሰረት በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በአፋር፣ በሶማሌ እንዲሁም በትግራይ የዕርዳታ አሰጣጡ ስራ መቀነሱ፣ ተረጂዎች ባሉባቸው ወረዳዎችና ቀበሌዎች በቂ የዕርዳታ እህል እየቀረበ አለመሆኑ፣ የሚመጣውም ዕርዳታ ፍትሐዊ በሆነ መልኩ ለተረጂዎች እየተሰራጨ አለመሆኑ አሳሳቢ ሆኖአል፡፡

No comments:

Post a Comment