Monday, January 25, 2016

በኮንሶ ታጣቂ ሃይሎች ህዝቡን በማዋከብ ላይ ናቸው

ኮንሶ ራሱን ችሎ በዞን ደረጃ ሊተዳደር ይገበዋል በሚል ህዝቡ ከወራት በፊት ያነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ የጸጥታ ሃይሎች የተለያዩ ወጣቶችና ጎልማሶችን ይዘው ካሰሩ በሁዋላ፣ ጥያቄው የአርበኞች ግንቦት 7 እንጅ የህዝቡ አይደለም ብላችሁ ፈርሙ በማለት ካለፉት 3 ሳምንታት ጀምሮ ቅስቀሳ ሲያካሄዱና ፊርማ ሲያሰባስቡ ቆይተዋል። ይሁን እንጅ ጥያቄው የአካባቢው ህዝብ በጉልበት ጥያቄያቸውን እንዲቀይሩ ለማድረግ እየተወሰደ ያለውን እርምጃ በመቃወማቸው፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የፌደራልና የደቡብ ክልል ልዩ ሃይሎች አካባቢውን ተቆጣጥረው ህዝቡን እየመረጡ ማሰር በመጀመራቸው፣ ነዋሪዎች ከአካባቢው እየሸሹ ነው።
የጸጥታ ሃይሎች የሚያደርሱትን ጫና በመቃወም ካለፉት ሶስት ሳምንታት ጀምሮ ትምህርት ቤቶች እና የተለያዩ መስሪያ ቤቶች መዘጋታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል። በዛሬው እለት በፋሻ ፣ ዱሪያና ኮልሜ ቀበሌዎች የልዩ ሃይል አባላት በሌሊት በመግባት ህዝቡን በመክበብ በግድ እንዲፈርም ለማድረግ ቢሞክሩም አልተሳካላቸውም።
የወረዳው የኢህአዴግ አባላት ጥያቄው የህዝብ ነው ብለው ጽፈው በመላካቸው ወቀሳ የደረሰባቸው ሲሆን፣ የወረዳው አፈጉባኤና ሌሎች የወረዳው ባለስልጣናትም ከስልጣን መነሳታቸውን ነዋሪዎች ተናግረዋል

No comments:

Post a Comment