Thursday, January 28, 2016

በኢትዮጵያ አንድ አምስተኛ የሚሆነው ሕዝብ ለረሃብ ሊጋለጥ ይችላል ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታወቀ

ጥር ፲፱ (አሥራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በሚልዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን በአሳሳቢ የርሃብ አደጋ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን በሚቀጥሉት ወራት አደጋው በእጥፍ እንደሚጨምር ቅድመ ጥናቶች አረጋግጠዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ግብረሰናይ የረድኤት ተቋማት በምስራቅ አፍሪካ ውስጥ ከተከሰተው የርሃብ አደጋዎች በኢትዮጵያ ያለው ርሃብ አድማሱን በማስፋቱ ከአጠቃላይ የአገሪቱ ሕዝብ ውስጥ አንድ አምስተኛ የሚሆነው ወይም ከ20 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው ህዝብ በርሃብ አደጋ ውስጥ እንዳለና ሁኔታዎቹ እየከፉ መምጣታቸውን ድርጅቱ አስታውቋል።
በአገሪቱ በተከሰተው የአየር መዛባት ሳቢያ ወቅቱን ጠብቆ ዝናብ ባለመዝነቡ በተከሰተው ድርቅ ሚሊዮኖች ለርሃብ ሲዳረጉ ሕጻናት ያልተመጣጠነ ምግብ በማጣታቸው ምክንያት የጤና መታወክ ደርሶባቸዋል። በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች በምግብ እጦት ምክንያት ልጆች ትምህርታቸውን ለማቋረጥ ተገደዋል።
ዓለምአቀፍ የረድኤት ድርጅቶች አፋጣኝ እገዛ እንዲያደርጉና ርሃብተኞችን እንዲታደጉ የተባበሩት መንግስታት ጥሪውን አቅርቧል።
በድርቁ ሳቢያ ከ100 ሽህ በላይ ኢትዮጵያዊያንና ሶማሊያዊያን ባሕር አቋርጠው ወደ የመን መግባታቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ቢሮ ገልጿል። በድርቁ ምክንያት ዕድሜያቸው ያልደረሱ ታዳጊዎች ካለ ዕድሜ ጋብቻ እንዲፈጽሙ በቤተሰባቸው እየተገደዱ መሆናቸውንም ድርጅቱ አስታውቋል።

No comments:

Post a Comment