Wednesday, January 13, 2016

የወልቃይትን ህዝብ ትግል የሚያስተባብሩ ሰዎች በጸጥታ ሃይሎች እየተዋከቡ ነው

ጥር ፬ (አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- “የወልቃይት ሕዝብ አማራነቱ ይከበርለት” በማለት ካለፉት ስድስት ወራት ወዲህ በፌዴራልና በአማራ ክልል እየቀረቡ አቤቱታ ሲያሰሙ የነበሩ የኮሚቴ አባላት ወደአካባቢቸው በሰላም ለመመለስ መቸገራቸው ታውቋል።
“የወልቃት ሕዝብ አማራ ነው፣ በትግራይ ክልል ሊተዳደር አይገባም” በማለት ጥያቄ ያነሱት ተወላጆች፣ የትግራይ ክልል አሁንም ጥያቄ የሚያቀርቡ ወገኖችን በተናጠልና በጋራ በማጥቃትና በማሳደድ ስራ በመጠመዱ ምክንያት የኮምቴ አባላቱ ያለስጋት ለመንቀሳቀስ አለመቻላቸው ታውቋል።
ባለፈው ህዳር ወር 2008 ዓ.ም የወልቃይት ተወካዮች በአዲስአበባ በመገኘት ቅሬታቸውን ለፌዴሬሽን ምክርቤት እና ለመንግስታዊው የሰብኣዊ መብት ኮሚሽን በጹሑፍ ያቀረቡ ሲሆን፣ በፌዴሬሽን ም/ቤት በኩል አቤቱታው በቅድሚያ ለትግራይ ክልል ቀርቦ በክልሉ በኩል ለፌዴሬሽን ም/ቤት መቅረብ እንዳለበት በቃል ምላሽ ማግኘታቸው ታውቋል፡፡
ሆኖም የኮሚቴ አባላቱ የማንነት ጥያቄውን ከአርበኞች ግንቦት ሰባት አባልነት ጋር አያይዞ ከሚያየው የትግራይ ክልል ጋር ለመነጋገር የደህንነት ዋስትና ችግር ስለገጠማቸው አቤቱታውን ለማቅረብ እንዳልቻሉ እየገለጹ ነው።
የወልቃይት ሕዝብ አማራነቱ እንዲከበር ለአማራ ክልል በተደጋጋሚ አቤቱታ ያቀረቡ ቢሆንም፣ የክልሉ መንግስት ችግሩን ለመፍታት አቅም ማነስ ብቻ ሳይሆን ጥያቄያችሁን አንሱ በማለት እያሳደረ ያለው ጫና ይበልጥ አበሳጭቷቸዋል።
የአካባቢው ሹማምንቶች ህዝቡ ትግራዋይነቱን እንዲቀበል ለማድረግ የጠሩት ስብሰባ በተቃውሞ ተበትኗል። የአካባቢው ህዝብ ምንም አይነት ስብከት አንቀበልም፣ ጥያቄያችንን ብቻ መልሱልን ማለቱን የደረሰን ዜና ያመለክታል።
ወልቃይት በሰሜን ተከዜ፣ በደቡብ ጠገዴ፣በምስራቅ የተከዜ ወንዝ፣ በምዕራብ አርማጮህና ሱዳን የሚያዋስኑት ሲሆን የአካባቢው ሕዝብ ባለፉት 23 ዓመታት የማንነት ጥያቄ አጠንክሮ በማቅረቡ ምክንያት ለእስርና ለሰብዓዊ መብት ረገጣ መጋለጡን ተወላጆች ይገልጻሉ።

No comments:

Post a Comment