Friday, January 8, 2016

በኦሮምያ የሚካሄደውን ተቃውሞ ተከትሎ የታሰሩት እንደፈቱ ሂውማን ራይትስ ወች ጠየቀ

ታኀሳስ ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የሰብአዊ መብት ድርጅቱ በምስራቅ አፍሪካ ተመራማሪው ፌሊክ ሆርን በኩል ባወጣው መግለጫ፣ የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ መታሰራቸውን ተከትሎ ግጭቱ እየተባባሰ መምጣቱንና በእስካሁኑ ተቃውሞ 140 ሰዎች መገደላቸውን ጠቅሷል።
አቶ በቀለ ገርባና ሌሎችም እስረኞች እንዲፈቱ የጠየቀው ሂውማን ራይትስ ወች፣ ዜጎች ሃሳባቸውን በነጻነት እንዲገልጹ እንዲፈቀድላቸው፣ አርሶአደሮችን በዘፈቀደ ማፈናቀል እንዲቆምና በቂ ምክክር እንዲደረግ አሳስቧል።
መንግስት ሰላማዊ ተቃውሞዎች እንዳይካሄዱ ባፈነ ቁጥር ዜጎች የ ሃይል አማራጭን ለመጠቀም እንደሚያዘነብሉ ያሳሰበው ሂውማን ራይትስ ወች፣ ይህ ደግሞ አገሪቱን ወደ አደገኛ አዙሪት የሚከታት እንዲሁም የረጅም ጊዜ ደህንነቷን አደጋ ውስጥ የሚከተው ነው ብሎአል።
በሌላ በኩል በገና በአል እለት ሳይቀር በክልሉ የሚካሄደው ተቃውሞ ተጠንከሮ ቀጥሎአል። በአሰቦት ከተማ አርሶደሮችና የከተማው ነዋሪዎች ባሰሙት ተቃውሞ የእለቱ ገበያ ፈርሷል። በፈንታሌ፣ ጊምቢ፣ አምቦና ፍቼም ህዝባዊ ተቃውሞ መደረጉን መረጃዎች ደርሰውናል። በትናንትናው እለት በሂርና በነበረው ተቃውሞ ደግሞ ወደ ሃረርና አጎራባች ከተሞች የሚሄዱ ነዋሪዎች መንገድ በመዘጋቱ ምክንያት የትራንስፖርት ችግር አጋጥሟቸው ነበር። አንድ ተሰፋሪ እንዳለው፣ በርካታ መንገደኞች ” የጸጥታ ችግር አለ በሚል” መንገድ ላይ ለማደር ተገደዋል።

No comments:

Post a Comment