Friday, January 8, 2016

አቶ በቀለ ነገአ በቁም እስር ላይ ናቸው

ታኀሳስ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኦፌዴን ሊቀመንበር አቶ በቀለ ነገአ በደህንነት ሃይሎች ታፍነው ተወስደው ድብደባ ከተፈጸመባቸው በሁዋላ፣ ከቤት ወጥተው ስራቸውን ለማከናወን ባለመቻላቸው በቁም እስር ላይ እንደሚገኙ ከባልደረቦቻቸው የተገኘው መረጃ አመልክቷል። ሌላው የድርጅቱ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ባልታወቀ ስፍራ ተወስደው የታሰሩ ሲሆን፣ አቶ በቀለ ነገአ ግን ማንኛውንም አይነት መግለጫ ለመገናኛ ብዙሃን እንዳይሰጡ እንዲሁም ከቤታቸው እንዳይወጡ በመከልከላቸው ጓደኞቻቸው በስልክ ከመጠየቅ በስተቀር በአካል አላገኙዋቸውም።
አቶ በቀለ በደህንነት ሃይሎች ታፍነው ከተወሰዱ በሁዋላ፣ በጻፉት ጽሁፍ ” ከእንግዲህ ለየትኛውም ሚዲያ ብትናገር እንገልሃለን፣ ለቤተሰቦችም ብታሰብብበት ይሻላል” እንዳሉዋቸው ገልጸው ነበር። ኢሳት አቶ በቀለን ለማግኘት ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም አልተሰካለትም።
በሌላ በኩል በኦሮምያ የሚካሄደው ተቃውሞ ዛሬም የቀጠለ ሲሆን፣ በምእራብ ሃረርጌ በ ጭሮ ወይም አሰበ ተፈሪ ህዝባዊ ተቃውሞ ሲካሄድ አርፍዷል።
በክልሉ የተነሳው ተቃውሞ ከ140 በላይ ሰዎችን መግደሉን ሂውማን ራይትስ ወች ቢገልጽም፣ መቀመጫውን አዲስ አበባ ያደረገው የአፍሪካ ህብረት እስካሁን መግለጫ አላወጣም። ይሁን እንጅ ህብረቱ ከጥር 12 እስከ 22 በአ/አ “የአፍሪካ የሰብአዊ መብት አመት” በሚል በተለይ በሴቶች መብት ላይ ያተኮረ ስብሰባ ለማካሄድ ማስታወቁን ገልጿል።ህብረቱ በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች በመንግስት ታጣቂዎች ስለተገደሉ እና በጅምላ ስለታሰሩ ዜጎች እንዲሁም በእስር ላይ ስለሚገኙ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች በማንሳት የኢህአዴግ መንግስትን ይወቅሳል ተብሎ አይጠበቅም።
ሂውማን ራይትስ ወች ያወጣው መግለጫ የአለማቀፍ መገናኛ ብዙሃንን ትኩረት ስቧል። ቢቢሰን ጨምሮ የተለያዩ አለማቀፍ የመገናኛ ብዙሃን የ140 ኢትዮጵያውያንን ግድያ ዘገባ ይዘው ወጥተዋል።
የአውሮፓ ህብረት በጉዳዩ ዙሪያ በሚቀጥለው ሳምንት ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ጉባኤም መግለጫ ይሰጣል ተብሎ እየተጠበቀ ነው።
ከምርጫ 97 በሁዋላ በተለያዩ ክልሎች ግድያዎች ቢፈጸሙም ፣በኦሮምያ የተካሄደው ጭፍጨፋ በ10 አመት ውስጥ ከታየው ከፍተኛው ነው።

No comments:

Post a Comment