Monday, January 4, 2016

የመንግስት ወታደሮች በኦሮምያ የሚፈጽሙትን ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ እንደቀጠሉ ነው

ታኀሳስ ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ለተከታታይ ሳምንታት በኦሮምያ የተደረገው ህዝባዊ ተቃውሞ ደም አፋሳሽ ሆኖ ቀጥሏል። የመንግስት ወታደሮች ያለርህራሄ በንጹሃን ዜጎች ላይ ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ እየወሰዱ ነው። እጅግ በጣም ዘግናኝ በሆነ መንገድ የተገደሉ ዜጎችን ምስል በማህበራዊ የመገናኛ ብዙሃን ማየት የተለመደ ክስተት ሆኗል። መንግስት የሚወስደው ከልክ ያለፈ እርምጃ ተቃውሞን ከመባባስ ውጭ ሊገታው አልቻለም።
በምእራብ ሃረርጌ በቆቦ ከተማ፣ በሂርናና አካባቢው ተቃውሞ ሲካሄድ ውሎአል። በአዳማ ዩኒቨርስቲ የሳይንስ ፋኩልቲ ደግሞ ተማሪዎች ተቃውሞዋቸውን ሲያሰሙ ውለዋል። የፌደራል ፖሊሶች ወደ ውስጥ በመግባት በተማሪዎች ላይ ጭካኔ የተሞላበት ድብደባ ፈጽመዋል። በርካታ ተማሪዎችም ተይዘው ታስረዋል። ትምህርትም ተቋርጧል።
አንዳንድ የፖለቲካ ድርጅቶች ከ100 ያላነሱ የክልሉ ነዋሪዎች በአጋዚ ወታደሮችና በፌደራል ፖሊስ አባላት መገደላቸውን ቢዘግቡም፣ በተለያዩ ቦታዎች ተገድለው የተጣሉ ዜጎች አሃዝ በውል አለመታወቁ የማቾችን ቁጥር ከዚህም በላይ ሊያደርሰው እንደሚችል ይናገራሉ።
ምንም እንኳ መንግስት በንጹሃን ዜጎች ላይ እያደረሰ ያለው አሰቃቂ ግድያ ተጠናክሮ ቢቀጥልም፣ የለአማቀፉ ማህበረሰብም ሆነ አለማቀፉ የመገናኛ ብዙሃን ብዙም ትኩረት አልሰጡትም። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ክፍልም ይሁን ሌሎች የተመድ አካላት እስካሁን ያወጡት መግለጫ የለም። የአሜሪካ መንግስትም ካወጣው ከአንድ የተለሳለሰ የአቋም መግለጫ ውጭ ሌላ መግለጫ እስካሁን አላወጣም:፡ የአውሮፓ ህብረትም በጉዳዩ ላይ ትኩረት አልሰጠም። ከአውሮፓ ኖርዌይ ዜጎቿ ወደ ኦሮምያ ክልል እንዳይጓዙ በድጋሜ አስጠንቅቃለች።

No comments:

Post a Comment