Thursday, December 28, 2017

አቶ በቀለ ገርባ ለምስክርነት የጠሯቸው የኦሮሚያ ክልል ባላስልጣናት ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠየቁ

አቶ በቀለ ገርባ ለምስክርነት የጠሯቸው የኦሮሚያ ክልል ባላስልጣናት ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠየቁ። ጥያቄውን ያቀረቡት በድርጅታቸው ኦህዴድ በኩል መሆኑ ታውቋል። በሚሰጣቸው ተለዋጭ ቀጠሮም በችሎት ቀርበው ምስክርነት እንደሚሰጡም ለፍርድ ቤቱ በጻፉት ደብዳቤ አስታውቀዋል። ከኦህዴድ ጽሕፈት ቤት ለፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 18/2010 በተጻፈው ደብዳቤ እንደተመለከተው አቶ በቀለ ገርባ በምስክርነት የጠሯቸው የክልሉን ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳን ጨምሮ አራት ባላስልጣናት ናቸው። ከአቶ ለማ መገርሳ በተጨማሪ የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር አብይ አሕመድ፣አፈ ጉባኤ አባዱላ ገመዳ እንዲሁም ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ የተባሉ የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት ናቸው ። ከኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ለፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተጻፈው ደብዳቤ ባለስልጣናቱ በቀጠሯቸው መገኘት ያልቻሉበትንና ተለዋጭ ቀጠሮ የጠየቁበትንም ምክንያት አስፍሯል። በአስቸኳይ ሀገራዊ ስብሰባ ምክንያት ቀርበው መመስከር ስለማይችሉ
የተከበረው ፍርድ ቤት ችግሩን በመረዳት ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ እንዲመቻችልንና ቀርበው እንዲመሰክሩ እንዲደረግልን የተለመደ የስራ ትብብራችሁን በአክብሮት እንጠይቃለን የሚለው በደብዳቤው ላይ የሰፈረው ጽሁፍ ነው። ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው በደብዳቤ የጠየቁትን የእነ ለማ መገርሳን ጉዳይ የተመለከተው ፍርድ ቤትም ለታህሳስ 27/2010 ብይን እሰጣለሁ በሚል ቀጠሮ ሰቷል። ዛሬ ችሎት ቀርበው በአቶ በቀለ ገርባ ላይ ምስክርነት ይሰጣሉ ተብለው ሲጠበቁ የነበሩት አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝም በተጣበበ ስራ ምክንያት መገኘት አልቻሉም በሚል በሳቸውም ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 27/2010 ቀጠሮ ተይዟል። ባለስልጣናቱ ተለዋጭ ቀጠሮ በጠየቁበት ሁኔታ በእነሱ ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ መያዙ ግን ግልፅ አይደለም ሲሉ የተከሳሾቹ ጠበቃ መናገራቸውን መረጃው አመልክቷል ። በባለስልጣናቱ የመከላከያ ምስክርነት አቀራረብ ላይ ብይን እሰጣለሁ በሚል ፍርድ ቤቱ ለታህሳስ 27/2010 ቀጠሮ ቢያዝም የተከሳሾቹን ጉዳይ ለማየት ግን ከየካቲት 5 እስከ የካቲት 9 ተከታታይ ቀጠሮ መቀመጡ ታውቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለም አቶ በቀለ ገርባ ለምስክርነት የጠሩትና በወህኒ ቤት የሚገኘው አቶ አንዱአለም አራጌን ወህኒ ቤቱ ለምስክርነት እንደማያቀረበው ለችሎቱ አስታውቋል። የቃሊቲ ወህኒ ቤት ሃላፊዎች አቶ አንዱአለም አራጌ ከባድ ፍርደኛ ስለሆነ እሱን ለምስክርነት ማቅረብ አንችልም ሲሉ ለፍርድ ቤቱ አስታውቀዋል። ፍርድ ቤቱም ለአቶ አንዱአለም አራጌ መጥሪውያው እንዲደርሰው በፖስተኛ ተላከ እንጂ አቅርቡት አላልንም የሚል ምላሽ መስጠቱን ጌታቸው ሽፈራው በማህበራዊ ገጹ ላይ አስፍሯል። አቶ አንዱአለም አራጌ የቀድሞ ቅንጅት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የነበረ ሲሆን በአንድነት ፓርቲ ውስጥ በምክትል ፕሬዝዳንትነት በማገልገል ላይ እያለ ከ6 አመት በፊት መታሰሩ ይታወሳል። የእድሜ ልክ እስራትም ተፈርዶበታል።

No comments:

Post a Comment