Thursday, December 14, 2017

አምቦ ዉስጥ መከላከያና ፖሊስ ተጋጩ (ፃዲቅ አህመድ)

«አጋዚዎች ሞተዋል» ሲሉ የአምቦ ምንጮች ለቢቢኤን ገልጸዋል።
 
የኦሮሚያና የአማራ ክልልሉ ተቃዉሞ አዲስ አበባ ቀርቧል። ሰበታ፣አለም ገና እና ፉሪ ተቃዉሞን ተቀላቅለዋል።«ተቃዉሞው አራት ኪሎ የቀረበ ይመስላል!» ይላሉ ሁናቴውን የቃኙ የቢቢኤን ምንጮች።
በአምቦ ከተማ ዉስጥ በመከላከያ ሰራዊትና በፖሊስ መካከል ግጭት ተነስቶ ከፍተኛ የተኩስ ልውውጥ እንደነበር የአምቦ ነዋሪዎች ለቢቢኤን ገለጹ።የመከላከያ ሰራዊቶቹ በዩንቨርስቲ ተማሪዎች ላይ በሚያደርሱት ትንኮሳና ጥቃት ሳቢያ ግጭቱ መነሳቱ ታዉቋል።የመከላከያ ሰራዊት በከተማዉ ጉዳዮች ዉስጥ የሚያደርገውን ጣልቃ ገብነት እንዲያቆም ፖሊስ ቢያሳስብም የመከላከያ ሰራዊቱ መቀበል ባለመቻሉ ጎራ ለይተው መታኮስ እንደጀመሩ ተገልጿል።
ቀደም ሲል መሳሪያዉን የፈታዉ የኦሮምያ ፖሊስ፤ መሳሪያን ዳግም በመታጠቁ የመከላከያ ሰራዊትን ጣልቃ ገብነትና ጥቃት ለማስቆም እየጣረ መሆኑ ተገልጿል።የአምቦ ነዋሪዎች ግጭቱ የቀሰቀሰው በመከላከያ ሰራዊት ነው በማለት ሒደቱን ያስረዳሉ።መንገድ የሚዘጉ ቄሮዎችን (ወጣቶችን) ለምን በቁጥጥር ስር አታዉሉም? በማለት አምቦ የተሰማራው የአጋዚ ሐይል አንድ ከፍተኛ መኮንን የከተማዉን ፖሊስ  በመዛለፉና የፓሊሱን ተኩሶ በማቁሰሉ ሳቢያ ሌላ ሴት ፖሊስ አጋዚዉን ከጀርባው ተኩሳ ገደለችው ሲሉ የከተማዉ እማኞች ይናገራሉ።ፖሊስና አጋዚ ጎራ በመለየት ሲታኮሱ የፌዴራል ፖሊስ ጣልቃ በመግባት ግጭቱን እንዳስቆመም ታዉቋል።
የአምቦ የዩንቨርስቲ ተማሪዎችን  የመከላከያ ሰራዊቱ ማደሪያ ክፍል (ዶርም) ድረስ በመግባት እየደበደበ ሁከት እንደሚፈጥር የከከተማዉ ነዋሪዎች አክለው ያስረዳሉ። የትግል ሰንደቅ አላማን፣ ለዉጥን በመሻት የሚደረጉ ድጋፎችን የሚያመላክት ጽሁፍንና በስልክ ዉስጥ ያለ መረጃን ለማየት የመከላከያ ሰራዊቱ ወጣቶችን እያስቆመ ስለሚፈትሽ  ዉጥረት መከሰቱ ታዉቋል።
በግጭቱ የሞቱት የመከላከያ ሰራዊቶች ቁጥር እስከ 10 ይደርሳል ቢባልም፤ ቁጥሩን ለማረጋገጥ አልተቻለም።ህዝቡ ከፍተኛ ብሶት ያለበት በመሆኑ የፖሊስ ሐይልን ተቀላቅለን አብረን የመከላከል ተግባሩን እንፈጽም በማለት ግፊት ቢያደርግም፤የፖሊስ ሐይሉ ግዜው ሲደርስ የህዝብን እርዳታ እንጠይቃለን በማለት ህዝብን እያረጋጋ እንደሚገኝ ታዉቋል።እንደ ከተማዉ ነዋሪዎች ገለጻ የኦሮምያ ፖሊስ ከመዘጋጀትም አልፎ በተጠንቀቅ ላይ ነው።
ቀደም ሲል የኦሮምያ ፖሊስ ትጥቅ የፈታ በመሆኑ መከላከያ ሰራዊት ሲመጣ ተገዶ የተዘጉ መንገዶችን ድንጋይና እንጨትን በማንሳት ይከፍት ነበር፣ አሁን ግን ከመከላከያው ሰራዊት እኩል የታጠቀ በመሆኑ የህዝብን ፍላጎት በማስጠበቅ ተግባር ላይ ተሰማርቷል በማለት የሚናገሩት የአምቦ ነዋሪዎች ብሶቱ ስር-የሰደደው በህዝቡ ዘንድ ብቻ ሳይሆን በፖሊሶቹም ጭምር መሆኑን ያስረዳሉ።
የአምቦ ህዝብና ፖሊስ ሰራዊቱ ሙሉ በሙሉ ተናበው ይሰራሉ የሚሉት የአምቦ ምንጮች፤ ህዝቡ በፖሊስ ላይ እምነት ባይኖረው ኖሮ ከተማዋ በተቃዉሞ ትቃጠል ነበር ሲሉ ሊከሰት የሚችለውን ነገር ያስረዳሉ ። የከፋ ነገር ከመጣ ህዝቡና የፖሊስ ሰራዊቱ በመጣምር ጥቃትን የመመከት ተግባር ላይ በመሰማራት የከተማዉን ደህንነት እንደሚያስጠብቅ አክለው ያስረዳሉ።
 
   የኦሮሚያና የአማራ ክልልሉ ተቃዉሞ አዲስ አበባ ቀርቧል
በሌላ በተያያዘ ዜና በኦሮሚያ ክልልና በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ እምቢተንነት ወደ አዲስ አበባ መቃረቡ ታወቀ። ሰበታ አካባቢ ያሉ የቢቢኤን ምጮች እንዳሳወቁት፤ ሰበታ ዉስጥ ህዝባዊ ተቃዉሞ በመነሳቱ ሳቢያ የፌዴራል ፖሊስ ስምሪት ጨምሯል። ሰበታ ዉስጥ ትምርት ቤቶች እንደተዘጉ የሚገልጹት እነዚሁ ምንጮች አለምገናና ፉሪም ተቃዉሞዉን መቀላቀላቸውንም ያስረዳሉ።
ተቃዉሞው አለምገና፣ ፉሪ ደረሰ ማለት «ለአራት ኪሎ ቀረበ» ማለት ነው የሚሉን ምንጮቻችን የአዲአ አበባ ህዝብ እየገሰገሰ ያለዉን ህዝባዊ እምቢተኝነት ተቀላቅሎ ለዉጥን እሙን ሊያደርግ ይገባል ሲሉ ተጣርተዋል።
አጋዚ የሚል መጠሪያ የተሰጠው፣ የህወሃትን ጥቅምና ስልጣን የሚያስጠብቀውና በጭካኔው የሚታወቀው ቅልብ ሰራዊት ከፖሊስ ሰራዊት ጋር እየተፋጠጠ ነው።የአምቦ የህዝብና ፖሊስ ተዋህዷል።ተቃዉሞው ወደ ወደ አዲስ አበባም ዳርቻ ቀርቧል።በአማራ ክልልና በኦሮሚያ ክልል የታየው አይነት ተቃዉሞ በሌሎች ክልልሎች ይስተዋል ይሆን በግዜ ሒደት ዉስጥ የሚታይ ይሆናል።

No comments:

Post a Comment