Tuesday, December 19, 2017

የሶማሌ ክልል ተወላጆች ለከፍተኛ አደጋ መጋለጣቸው ተገለጸ

(ኢሳት ዲሲ--ታህሳስ 10/2010) ከ5ሺህ በላይ የሶማሌ ክልል ተወላጆች በምዕራብ ሀረርጌ ዞን በተለያዩ ቀበሌዎች ውስጥ ያለውሃና ምግብ በመቆየታቸው ለከፍተኛ አደጋ መጋለጣቸው ተገለጸ። 
ሰሞኑን ከተከሰተው ግጭት ጋር በተያያዘ የስልክም ሆነ የትራንስፖርት ግንኙነት ተቋርጧል።
አስቸኳይ ድጋፍ ካልደረሰላቸው ዕልቂት ሊከሰት እንደሚችል በማስጠንቀቅ የሶማሌ ተወላጆች የአክቲቪስቶች መረብ መግለጫ አውጥቷል። 
በአራት ቀበሌዎች ተጠልለው የሚገኙ የሶማሌ ተወላጆችን ለመደገፍ የኦሮሞ ሽማግሌዎችና ወጣቶች ጥረት እያደረጉ መሆኑም ተገልጿል።
በአካባቢው ሌላ ዙር ጥቃት ይፈጸማል የሚል ስጋት እንዳለም ለማወቅ ተችሏል።
በምዕራብ ሀረርጌ ዞን በቆርኬ፣ በዳባ፣ በዋታራራና በሚሊቃዪ ቀበሌዎች ከ5ሺህ በላይ የሶማሌ ተወላጆች የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ መሆናቸው ታውቋል።
የሶማሌ ተወላጆቹ ምግብና ውሃ ካገኙ ቀናት እንዳለፋቸው እየተነገረ ነው። ህክምና አላገኙም።
ከምግብ እጥረት ጋር በተያያዘ በሚከሰቱ በሽታዎች ህጻናት እየተሰቃዩ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።
የሶማሌ አክቲቪስቶች መረብ ሰብሳቢ አቶ ጀማል ዲሪዬ እንደሚሉት ሁኔታዎች አሳሳቢ ናቸው። ስርዓቱ ምን ዓይነት ተንኮል እያሰበ እንዳለ ለማወቅ አልቻልንም።

ባለፈው ቅዳሜ በምዕራብ ሀረርጌ ዞን በጋዱሎ ወራድ በተፈጸመ ጥቃት ከ100 በላይ የሶማሌ ተወላጆች መገደላቸውን ተከትሎ አካባቢው በከፍተኛ የጸጥታ ስጋት ውስጥ እንዳለ ይነገራል።
የህወሃት መንግስትም በይፋ እንደገለጸው የተፈጠረው ግጭት አጠቃላይ የሰላሙን ሁኔታ አደጋ ውስጥ ከቶታል።
ጥቃቱ አሁንም እንዳልቆመ ከሚደርሱን መረጃዎች ለማወቅ ተችሏል።
የመከላከያ ሰራዊትም ሆን ተብሎ ከአካባቢው እንዲወጣ መደረጉን ተከትሎ እግር በእግር ተክተው በገቡ ሃይሎች የተፈጸመው ጥቃት ወደሌሎች ቀበሌዎችም እንዳይዛመት ምንም ዓይነት ጥረት እየተደረገ እንዳልሆነ በመገለጽ ላይ ነው።
በ4ቱ ቀበሌዎች ያለውሃ፣ ምግብና ህክምና ቀናት ያለፋቸውን የሶማሌ ክልል ተወላጆችን ለመርዳት በአካባቢው የኦሮሞ ሽማግሌዎችና ወጣቶች ጥረት እየተደረገ መሆኑን አቶ ጀማል ገልጸዋል።
ጥቃቱ በተፈጸመባቸው በእነዚህ ቀበሌዎች ምንም ዓይነት የመንግስት መዋቅር አለመኖሩ ነው የተገለጸው።
ለኢሳት የሚደርሱ መረጃዎች እንደሚያመለክቱትም በምዕራብ ሀረርጌ ችግሩ በተፈጠረባቸው አካባቢዎች አሁንም ሰዎች እየተገደሉ ነው።
የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር ድርጊቱ መፈጸሙን ጠቅሶ በኦሮሞ ተወላጆች ላይም ተመሳሳይ ጥቃት ተፈጽሞ በርካታ ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል።
አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ባለፈው ዕሁድ በሰጡት መግለጫ በኦሮሚያ ፖሊስ ጣቢያ በተጠለሉ ሰዎች ላይ ጭፍጨፋ መፈጸሙን ጠቅሰዋል።
የሶማሌ ክልል ኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት በበኩሉ መከላከያ ሰራዊት ከወጣ በኋላ ድርጊቱ ተፈጽሟል ሲል ገልጿል።
የብዙዎች ጥያቄ በቀጠናው ውጥረቱ በበረታበት ወቅት የመከላከያ ሰራዊት አከባቢውን ጥሎ እንዲወጣ የተደረገው ለምንድን ነው የሚል ሆኗል። መልስ እስከአሁን አልተገኘለትም።

No comments:

Post a Comment