Tuesday, December 19, 2017

ስኳር ኮርፖሬሽን ተበላሽቶ ቀብሬዋለሁ ያለው ሁለት መርከብ ስኳር የሃሰት መሆኑን ምንጮች አስታወቁ

በስኳር ኮርፖሬሽን በውጭ ምንዛሬ ተገዝቶ በሁለት መርከብ ተጭኖ ወደ አገር ውስጥ አስገብቸዋለሁ ያለው 3 ሺህ 777 ኩንታል በመበላሸቱ መተሃራ ውስጥ ቀብሬዋለሁ ያለው ስኳር የሃሰት መረጃ መሆኑን ምንጮቻችን አስታውቀዋል።
አገኘሁ ጌታቸው ተጨማሪ አለው
ኮርፖሬሽኑ ለስኳሩ መበላሸት የኢትዮጵያ ንግድ መርከብን በምክንያትነት ቢያቀርብም በንግድ መርከብ ተጭኖ ስኳሩ አገር ውስጥ ኮርፖሬሽኑ እስኪረከበው ድረስ ምንም ዓይነት የጥራት መጓደል እንዳልነበረው ምንጮች አክለው ገልጸዋል።
ስኳር ኮርፖሬሽኑ ባለስልጣናት ስኳሩን የቀበርነው ውጭ አገር ድረስ ልከን መበላሸቱንና ለምግብነት እንደማይውል ካረጋገጥን በኋላ ነው። ስኳሩ ሲቀበር ምስክር እንደነበራቸው ለፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ያቀረቡት መረጃ ፍጹም ታአማኒነት የሌለው ሪፖርት መሆኑን ምንጮቻችን ገልጸው ስኳር ኮርፖሬሽን ስኳሩን ከተረከበ በኋላ ተበላሽቶ መቅበሩን መግለጹ በመተሃራ ስኳር ፋብሪካ አመራሮች ዘንድ ግርምትን ፈጥሯል።
ከተወሰኑ ዓመታት ወዲህ በሙያቸው ለረዥም ዓመታት በመተሃራ ስኳር ፋብሪካ ውስጥ ተቀጥረው ሲያገለግሉ የነበሩ ባለሙያዎችን በማግለል የህወሃት ታማኞችን በከፍተኛ አመራርነት መሾም እየተለመደ መጥቷል። ይህም በድርጅቱ ሰራተኞች ዘንድ ከፍተኛ ቅሬታን ፈጥርዋል።
የደመወዝ እድገትን ጨምሮ በዓመቱ መጨረሻ ይሰጡ የነበሩ ልዩልዩ ጥቅማጥቅሞች እንዲዘገዩ ከመደረጋቸው በተጨማሪ ለፋብሪካው የሚደረግለት እድሳት በመለዋወጫ እጥረት ምክንያት እንዲዘገይ ተደርጓል። ስኳር በአገር ውስጥ ከፍተኛ እጥረት እያለና ፋብሪካው ምርቱን ሳያቆም ለምን ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ እንዲያመርት አልተደረገም? ሲሉ ሰረተኞች ለአመራሩ ጥያቄዎችን ቢያቀርቡም አሳማኝ ምላሽ አላገኙም።

በተጨማሪም የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት በስኳር ኮርፖሬሽን ፕሮጀክቶች መጓተታቸውን ተከትሎ ከፍተኛ የአገር ሃብት በመባከኑ ምርመራ ሊደረግባቸው ይገባል ብሏል። እንደ ኦዲተር መስሪያ ቤቱ ሪፖርት የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ አፈጻጸምን አስመልክቶ ዓመታዊ የግርድፍ መሬት፣ የውሃ ገብ መሬት ርክክብና የሸንኮራ አገዳ ተከላ እቅዶች አለመሳካታቸውን አስታውቋል። የፋብሪካው ግንባታና ተከላ በ6 ዓመት መዘግየቱ፣ የእርሻ ዘርፍ እቅድ አፈፃፀም የሸንኮራ አገዳ የመስኖ ልማት፣ የመሬት ድልዳሎአነስተኛ መሆኑ፣ ለፋብሪካው በአማካሪነት ከተቀጠረው ድርጅት ጋር የተገባው ውል ለ7 ዓመታት መራዘሙና ይህም ወደ 9.5 ሚልየን ብር ጭማሪ (713.4%) እንዲከፈል ማድረጉንና ለ499 ቤቶች ግንባታ ከ300 በላይ ለሆኑ ተቋራጮች ካለ ውል ስራ መሰጠቱ በኦዲት ተረጋግጧል።
ከዚህ በተጨማሪም በርካታ ዘመናዊ ማሽነሪዎች በብልሽትና በመለዋወጫ እጥረት አገልግሎት የማይሰጡ መሆናቸውና ይህም ለኪራይ ለሚወጣ ለተጨማሪ ወጪ ፋብሪካው ተዳርጓል። ከብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሜቴክ ለማሽነሪ ግዥ 44 ሚሊዮን ብር ውል ቢፈጸምም ከውሉ ጊዜ በላይ በአንድ ዓመት መዘግየቱ እንዲሁም ከአገልግሎት ውጪ የሆኑና ያልተወገዱ ቋሚ ንብረቶች መኖራቸው በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
ለሸንኮራ አገዳ ልማት የቲሹ ካልቸርን ስራ ላይ ለማዋል ስለተመደበው በጀትና ስለወጣው ወጪ ምን ያህል መሆኑን ማወቅ አልተቻለም። ፋብሪካው ምርት ባለመጀመሩ በ2008 ዓ.ም በጀት ዓመት የቆረጣ ጊዜ ያለፈበት 303.17 ሄክታር የሸንኮራ አገዳ እንዲገለበጥ ተደርጓል። በአገዳ ዕድሜ እርጅና ምክንያት በ1 ሽህ 50 ሄክታር ላይ የተተከለ ሸንኮራ አገዳ ሙሉ በሙሉ መወገዱና ፋብሪካው አገዳን ተቀብሎ ባለመፍጨቱ 800 ሄክታር መሬት ዕድሜው ባለፈ የሸንኮራ አገዳ መሸፈኑ በኦዲት ግኝትነት ተጠቅሰዋል፡፡
በመተሀራ ስኳር ፋብሪካ ረገድ የኢታኖል ፕላንት ግንባታና ተከላ ጨረታ ሂደትን የሚያሳይ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ሰነድ አልተገኘም። ለግንባታና ተከላ ከተመደበው መነሻ የኮንትራት ዋጋ በላይ በብልጫ ለተፈጸመው 33 ሚሊዮን 859 ሽህ 495.41 ብር ክፍያ ምክንያቱን የሚገልጽ የውል ማስረጃ አለመቅረቡና ፕሮጀክቱም ከማጠናቀቂያ ጊዜው በ4 ወር ዘግይቷል። በመለዋወጫ እጦት ኢታኖል ለማምረት የሚያስፈልገውን የእንፋሎት ሀይል ማቅረብ ባለመቻሉ ከምርት ሊገኝ የሚቻል ከ68,6 ሚልየን ብር በላይ መታጣቱ እንዲሁም በግብዓትነት ሊውል የሚችል ግምቱ 39 ሚሊዮን 193 ሽህ 770 ብር የሚያወጣ ሞላሰስ ባክኗል።
ግምቱ ከ3 ሚንሊዮን 915 ሽህ 328.10 ብር የሚያወጣ ከተሽከርካሪዎች ነዳጅ ጋር የሚቀላቀል 412 ሽህ 139.8 ሊትር ኢታኖልና ለተለያዩ የመጠጥ ኢንዱስትሪዎች በግብዓትነት የሚሸጥ 2 ሚሊዮን 559 ሽህ 388.99 ብር የሚያወጣ 176 ሽህ 631.4 ሊትር ረክቲፉይድ ስፕሪት አልኮል ባለመመረቱ በድምሩ 6 ሚሊዮን 474 ሽህ 717.09 ብር ሀገሪቱን ማሳጣቱን በኦዲት ሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
ከስኳር ኮርፖሬሽኑ ግዥ አፈፃፀም መመሪያ ውጪ በውል ያልታሰሩ ግዥዎች ተፈርጽመዋል። ለሥራ ላይ አደጋ መከላከያ አልባሳት ተብሎ ተጨማሪ 168 ሽህ 834.89 ብር ለሠራተኞች ዩኒፎርም ግዥ ደግሞ 437 ሽህ 368.75 ብር ተጨማሪ ወጪ ለሁለት አቅራቢዎች እንደከፈለ በሪፖርቱ ለብነት ተጠቅሷል፡፡
የእንፋሎት ሀይል ለማመንጨት የሚያስፈልገውን ውሃ እንዲያጣራ 1 ሚሊዮን 906 ሽህ 362 ብር ለፋብሪካው ተገዝቶ ከህንድ የመጣና ሌሎች ልዩ ልዩ ክፍያዎች ተፈጽመውለት የተተከለው መሳሪያ ፋብሪካው ከሚጠቀምበት ነባር ቴክኖሎጂ ጋር ባለመግጠሙ ምክንያት ከሁለት ዓመታት በላይ አገልግሎት ሳይሰጥ ተቀምጧል። በ2013/2014 እ.ኤ.አ. በጀት ዓመት 2 ሚሊዮን 743 ሽህ 242 ብር ለሚያወጡ ግዥዎች አግባብ ባልሆነ ሁኔታ መፈሰማቸውን ተከትሎ በተደረገ የማጣራት ጥረት 480 ሽህ 533.67 ብር ማስመለስ ቢቻልም 2 ሚሊዮን 262 ሽህ 708.33 ብር እስካሁን ድረስ ያልተመለሰ መሆኑን ኦዲቱ አሳይቷል፡፡
በፋብሪካው በ2012 እስከ 2014 እ.ኤ.አ. ባሉት ሁለት የበጀት ዓመታት ውስጥ በተደረጉ ዓመታዊ የንብረት ቆጠራ በርካታ ንብረቶች ያልተገኙ በሚል በቋሚ ንብረት መዝገብ ላይ ቢመዘግብም ምንም የማስተካከያ እርምጃ አልተወሰደም።
በእርጅናና በተለያዩ ምክንያቶች ከአገልግሎት ውጪ የሆኑ በርካታ የነባር የስኳር ፋብሪካዎች ቋሚ ንብረቶች አለመወገዳቸው፣ በተደረገው የነዳጅ ቆጠራ 3 ሽህ 224.86 ሊትር ፔትሮሊየም እና 8 ሽህ 304.95 ሊትር ዲዝል ከካርድ ባላንስ ጋር ሲነፃፀር አንሶ ተገኝቷል።
ኮርፖሬሽኑ የወንጂ ሸዋ ስኳር ፋብሪካ ግንባታ ዲዛይንና ዝርዝር የኢንጂነሪንግ ፓኬጅ አቅርቦትን፣ ማንዋሎችንና የመለዋወጫ ስፔስፊኬሽኖችን በውሉ መሠረት ከተቋራጩ አልተረከበም። የስኳር ፋብሪካ ማስፋፊያ የመነሻ ውል ስምምነት ላይ የፋብሪካው መጠናቀቂያ ጊዜ አልተገለጸም። የፋብሪካ ግንባታና ተከላ ስራውን በአማካሪነት የተከታተለው ኩባንያ ውል ማጠናቀቂያ ጊዜ ለ8 ጊዜ እየተራዘመ ለ9 ዓመታት ዘግይቷል። በዚህም ምክንያት 4 ሚሊዮን 648 ሽህ 860 ዩሮ ተጨማሪ ክፍያ ለኩባንያው መከፈሉን ኦዲቱ አመልክቷል፡፡
የወለንጪቲ ቦፋ መስኖ ፕሮጀክት በ3 ዓመት ለማጠናቀቅ ውል ቢገባም ለ2 ዓመት ከ2 ወር ዘግይቷል። የግንባታው አማካሪ ሆኖ የሰራው የውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅት የመነሻ ኮንትራት ውል ለ24 ወራት የሚያገለግልና እንደየአስፈላጊነቱ የሚታደስ ሆኖ የመነሻ ኮንትራት ውል 17 ሚሊዮን 427 ሽህ 728.99 ብር የተፈረመ ቢሆንም ስራዎቹ በተቀመጠላቸው የጊዜ ባለመጠናቀቃቸው ውሉ 4 ጊዜያት ታድሷል። በዚህ በድምሩ 30 ሚሊዮን 489 ሽህ 214 ብር ከመነሻ ዋጋ ተጨማሪም ክፍያ እንዲፈጸም ተደርጓል።
ጂቡቲ ወደብ ተከማችተው የሚገኙ የፋብሪካ እቃዎችን በተመለከተ በፋብሪካው ለኮርፖሬሽኑ የቀረቡ የድጋፍ ጥያቄዎች ምላሽ አላገኙም። ከሞጆ ደረቅ ወደብ ለሚመጡ ዕቃዎች 22 ሚሊዮን 019 ሽህ 678.78 ብር መከፈል ባለመቻሉ ለመጋዘን ኪራይ 393 ሽህ 231.33 ብር መከፈሉም ተመልክቷል፡፡
በ2014 /2015 እ.ኤ.አ የበጀት ዓመት 124 ቀላል እና 41 ከባድ ተሽከርካሪዎች፣ በ2015/2016 እ.ኤ.አ. በጀት ዓመት ደግሞ 172 ቀላልና 21 ከባድ ተሽከርካሪዎች በንብረት ቆጠራ ወቅት አልተገኙም። የፋብሪካው የነዳጅ አጠቃቀም ከበጀት መጠኑ በላይ መሆኑን የውስጥ ኦዲት ሪፖርቱ ያሳያል። በተጨማሪም በእርጅናና በተለያዩ ምክንያቶች ከአገልግሎ ውጪ የሆኑ ቋሚ ንብረቶች አለመወገዳቸው በኦዲቱ ታውቋል፡፡
በአካባቢ ጥበቃ ረገድም በፋብሪካው የሰራተኞች መኖሪያ መንደር 18 አካባቢም የአካባቢውን ሙቀትና ንፋስ ለመቀነስ የሚያችል የዛፍ ተከላ ሽፋን እንደሌለ ኦዲቱ አመልክቷል፡፡ በፋብሪካው የአገዳ አቅርቦት፣ በጥገና ጋራዥ እንዲሁም በአካባቢው በሚገኙት መንገዶች በሚነሳ አቧራ ብናኝ ሠራተኛው በጤና መታወክ ላይ መሆኑን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ሪፖርት አትቷል።
እስካሁን ሪፖርቱን ተከትሎ በስኳር ኮርፖሬሽኑ ላይ በቀረቡት የአሰራር ድክመቶችና በወደመው ከፍተኛ መጠን ያለው የአገር ሃብት ተጠያቂ የሆኑ የመንግስት ባለስልጣናት የሉም።

No comments:

Post a Comment