Thursday, December 14, 2017

በሽብር ስም የተከሰሱ ሰባት እስረኞች በነፃ ሲሰናበቱ ዘጠኙ እንዲከላከሉ ተባሉ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 5 ቀን 2010 ዓ.ም በዋለው ችሎት በእነ ተሾመ ረጋሳ የክስ መዝገብ ስር በሽብር ስም ተከሰው የነበሩ 7 ግለሰቦችን በነፃ ተሰናበቱ። 9 ተከሳሾች ደግሞ በተከሰሱበት ክስ ከባድ ቅጣት በሚያስቀጣ አንቀፅ ስር እንዲከላከሉ ተበይኖባቸዋል።
1ኛ ተከሳሽ የሆኑት አቶ ተሾመ ረጋሳ ላይ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ የተቀሰቀሰውን አመፅ በአማራና በትግራይ ክልሎች በተለይም ጎንደር፣ መተማ፣ ሁመራ፣ ደሴ፣ መቀሌ፣ አክሱምና ሌሎች ከተሞች ለማስፋፋት አቅዶ እየሰራ ነበር ሲል ዐቃቤ ሕግ ክስ መስርቷል።
በተጨማሪም በአቶ ተሾመ ረጋሳና አብረውት በተከሰሱት ተከሳሾች ላይ የኢትዮጵያ መንግስት በኦሮሞ ህዝብ ላይ በደል ፈፅሟል፣ ኦህዴድ አይወክለንም፣ መሬት እየተሸጠ ነው።ወጣቶች የኦህዴድን ሰንደቅ አላማ አውርደው የኦፌኮን ሰንደቅ አላማ ለማስቀል ጥት አድርገዋል፣ ኦነግ ስልጣን እንዲረከብ ይፈልጋሉ የሚሉ ክሶች ቀርቦባቸዋል።
ነገርግን ዐቃቤ ሕግ በ5ኛ፣ 6ኛ፣ 7ኛ፣ 9ኛ፣11ኛ ፣13ኛ እና 15ኛ ተከሳሾች ላይ ያቀረበው ክስ አስመልክቶ ችሎቱ የሰውም ሆነ አሳማኝ የሰነድ ማስረጃ አላቀረበም ተብሏል። በመሆኑም 5ኛ ተከሳሽ ከበደ ጨመዳ፣ 6ኛ ተከሳሽ ዴቢሳ በየነ፣ 7ኛ ተከሳሽ ምህረቱ ጉልማ፣ 9ኛ ተከሳሽ መንግስቱ ጉዲሳ፣ 11ኛ ተከሳሽ ቦንሳ ኃይሉ፣ 13ኛ ተከሳሽ ጃራ ኤቢሳ እና 15ኛ ተከሳሽ አጥናፉ ቢረሳ የቀረበባቸውን ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ሲል ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጥቷል።

1ኛ ተከሳሽ አቶ ተሾመ ረጋሳ እና 16ኛ ተከሳሽ አቶ አብዲ ታደሰ ተጠቅሶባቸው በነበረው አንቀፅ 3(1) እና (4) ስር እንዲከላከሉ ፍርድ ቤቱ በይኗል። በተመሳሳይ አንቀጽ ተከሶ የነበረው 4ኛ ተከሳሽ አቶ ኒሞና ለሜሳ በበኩሉ ክሱ ወደ አዋጁ አንቀፅ 4 ተቀይሮ ይከላከል ተብሏል። 2ኛ ተከሳሽ አቶ ጫላ ድኤሳ፣ 3ኛ ተከሳሽ አቶ ኦብሱማን ኡማ፣ 8ኛ ተከሳሽ አቶ ጌታሁን ደስታ፣10ኛ ተከሳሽ አቶ ተሰማ ሁንዴ፣12ኛ ተከሳሽ አቶ አሸብር ኦንቾ እና 14ኛ ተከሳሽ አቶ ፉፉ በተከሰሱበት አንቀፅ 4 ስር እንዲከላከሉ ተበይኖባቸዋል።
ተከሳሾቹ ተከላከሉ የተባሉበት አንቀፅ ከ15 ዓመት እስከ እድሜ ልክና ሞት ድረስ የሚያስቀጣ አንቀጽ ነው። አብዛኛዎቹ ተከሳሾች የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ (ኦ.ፌ.ኮ.) አባልና ከፍተኛ አመራር ናቸው። አቶ አሸብር ኦንቾ የመሰናዶ እንዲሁም አቶ ጫላ ድኤሳ የአምቦ ዩኒቨርሲቲ መምህር ናቸው። ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ የተበየነባቸው አንቀጽ ላይ መከላከያ ምስክር ለማቅረብ ለጥር 24 ቀን 2010 ዓ.ም ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል። 3ኛ ተከሳሽ የሆኑት አቶ ኦብሱማን ኡማ በቀረበበት ክስ ላይ እንደማይከላከል ለችሎቱ አሳውቋል።
በአርበኞች ግንቦት ሰባት ስም ክስ የቀረበባቸው በእነ ፈለቀ አባብዬ የክስ መዝገብ የተከሰሱት አቶ ፈለቀ አባብዬ፣ አቶ ዋሴ ታደሰ፣ አቶ ገደፋዬ ወርቁ እና አቶ ፋንታሁን አበበ በግላቸው ጠበቃ ማቆም ባለመቻላቸው መንግስት ጠበቃ አቁሞላቸው ነበር።
ተከሳሾቹ መንግስት ያቆመላቸው ጠበቃ ቀርቦ ሊያማክራቸው ባለመቻሉ ''ያቆመልንን ጠበቃ አንፈልግም በግላችን እንከራከራለን'' ሲሉ ለችሎቱ አሳውቀዋል። የቀረበባቸው የክስ አንቀፅ ከባድ ቅጣት የሚያስቀጣ ስለሆነ በጠበቃ መታገዝ እንዳለባቸው ከችሎቱ ቢነገራቸውም ጠበቃቸው ጉዳያቸውን እያሰፈፀመላቸው ስላልሆነ እንደማይፈልጉት ገልጸዋል። 1ኛ ተከሳሽ አቶ ፈለቀ አባብዬ መንግስት አቁሜልሃለሁ ያለውን ጠበቃ እንደማይፈልጉት ከመግለጻቸው በተጨማሪ በችሎቱና በፍትሕ ስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ለችሎቱ አሰምቷል።
1ና ተከሳሽ አቶ ፈለቀ አባብዬ ''ጨለማ ቤት ውስጥ ብቻየን ታስሬ ነበር። የሰው ልጅ ይደርስበታል ተብሎ የማይታሰብ ስቃይ ደርሶብኛል። ማስረጃ የት ተገዝቶ እንደሚመጣም አውቃለሁ። ይህን ችሎት ገለልተኛ ነው ብየ አላምንም። ጉዳዬን እንዲያይልኝ የምፈልገው ችሎት እንጅ ቡድን አይደለም። እኔ የተከሰስኩት አማራ ስለሆንኩ ብቻ ነው። አማራን ሲያወግዝ የነበረና ሌሎች ይነሳልን ያሉት ዳኛ ጉዳዬን ሊያይልኝ አይችልም። ውሳኔዬ በማረሚያ ቤት ይምጣልኝ" ሲል በፍርድ ቤቱ የተሰየሙት ዳኞች ገለልተኛ አለመሆናቸውን አሳውቋል።
የተከሳሹን መቃወሚያ ከሰሙ በኋላ ዳኛው በበኩላቸው " አንተ ፈለግክም አልፈለግክም ይታያል። ከሳሽ እስካለ ድረስ በዚሁ ችሎት ይታያል።" የሚል ምላሽ ሰጥተውታል።
በእነ አቶ ፈለቀ አባብዬ ላይ ለመመስከር አስር የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች የተቆጠሩ ሲሆን ሶስቱ ፈርመው ሲቀሩ ሳጅን አገኘሁ አቻው የተባለ ግለሰብ ብቻውን ለመመስከር ቀርቧል። ዋና ሳጅን አገኘሁ አቻው በበርካታ ክሶች ዝርዝር ላይ ዋና ተዋናኝ ተደርጎ የተጠቀሰ ቢሆንም በሌሎች ተከሳሾች ላይ እመሰክራለሁ በማለቱ ሳይከሰስ ማዕከላዊ እንደሚገኝ ምንጮች ይገልጻሉ። ምስክሩ በቀጣይ ቀጠሮ ይቀርባል ተብሎ በችሎት የተነገው ሲሆን ከማዕከላዊ ፓሊሶች ጋር በተቋሙ መኪና እንዲመለስ ተደርጓል። በሽብር ተጠርጥሮ በሌሎች ላይ ለመመስከር የተስማማ ተጠርጣሪ ክስ ሳይቀርብበት መስክሮ ከእስር እንደሚፈታ ይታወቃል።
በርካታ በሽብር ስም አገዛዙ ክስ ያቀረበባቸው ተከሳሾች በግላቸው ጠበቃ የማቆም አቅሙ የሌላቸውም። ከመንግስት የሚመደቡላቸው ጠበቆች በበኩላቸው እስር ቤቶች ድረስ በመምጣት የማማከር አገልግሎት አይሰጡንም። በተገቢው መልኩ ሕጉን ተከትለው አይከራከሩልንም ሲሉ ተከሳሾች ይወቅሳሉ። በተለይ በዓርበኞች ግንቦት ሰባት ስም የሚከሰሱት አብዛሃኞቹ ተከሳሾች ያለ ጠበቃ መከራከርን ይመርጣሉ።

No comments:

Post a Comment