Tuesday, December 19, 2017

በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ውጥረት ተከትሎ በተለይም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የመከላከያ ሰራዊት ጣልቃ እንዲገባ በሃይማኖት አባቶች ስም እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መሆኑ ታወቀ።

በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ውጥረት ተከትሎ በተለይም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የመከላከያ ሰራዊት ጣልቃ እንዲገባ በሃይማኖት አባቶች ስም እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መሆኑ ታወቀ። የኢሳት ምንጮች ከአዲስ አበባ እንደገለጹት የመከላከያ ሰራዊት ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ያለ ክልሉ ፈቃድ እንዲገባ የሃይማኖት አባቶች ጥሪ እንዲያደርጉ ታዘዋል። የሃይማኖት አባቶች በቀጣዮቹ ቀናት በዚህ ዙሪያ የጋራ መግለጫ እንደሚሰጡ ይጠበቃል። በፌደራልና በአርብቶ አደሮች ሚኒስቴር በኩል ለቀረበው ጥያቄ የሕወሃትና ሌሎች ከሕወሃት ጋር በቅርበት የሚሰሩ ባለስልጣናት ለሃይማኖት አባቶቹ በስልክና በአካል ስለጉዳዩ ማብራሪያ እየሰጡ መሆናቸውን ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል። የሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ/ሕወሃት መሪዎች በፓርቲያቸው ውስጥ ሹምሽር ባደረጉ ማግስት በአጋር ፓርቲዎች ውስጥም በተመሳሳይ ብወዛ በማድረግ ሁሉን ነገር ለመቆጣጠር የነበራቸው እቅድ በኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናትና በተወሰኑ የብአዴን አመራሮች ተቃውሞ መገታቱን ለማወቅ ተችሏል። እየተካሄደ ባለውና ዛሬ ሳምንቱን ባስቆጠረው የኢሕአዴግ ስራ አስፈጻሚ ስብሰባ አብዛኞቹ የኦህዴድና አንዳንድ የብአዴን መሪዎች በያዙት ጠንካራ አቋም ሳቢያ ሕወሃት ክልሎችን በወታደራዊ
ሃይል ለመቆጣጠር እየተንቀሳቀሰ እንደሆነም ተመልክቷል። የሃይማኖት አባቶቹ ጥሪ እንዲያደርጉ የተፈለገውም ሕወሃት በክልሎች ለሚያደርገው ጣልቃገብነት ሽፋን እንዲሰጡት እንደሆነም መረዳት ተችሏል። የሀገሪቱ ፖለቲካዊ ሁኔታ እንዲህ በተወጣጠረበት ወቅት በሕወሃት የጦር ጄኔራሎች የሚታዘዘው የመከላከያ ሰራዊት ወደ ክልሉ ቢገባ ቀውሱ ይበልጥ እንደሚባባስና ከቁጥጥር ውጭ የሆነ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል የፓለቲካ ምሁራን ይናገራሉ። የሃይማኖት አባቶቹ ግልጽ ባልሆነና ባልረጋ የፖለቲካ ሂደት ውስጥ የትኛውንም ወገን ደግፈው የሚሰጡት መግለጫ ችግሩን ከማባባስ ባሻገር የሀገሪቱን ቀውስ በሽምግልና ለመፍታት የሚኖራቸውን ክብርና ተሰሚነት የሚያሳጣ ኣንደሚሆንም የፖለቲካ ባለሙያዎች ስጋታቸውን ይገልጻሉ።

No comments:

Post a Comment