Friday, December 22, 2017

የፌደራል ጠ/አቃቢ ህግና የህወሃት ጄኔራሎች በሶማሊ ክልል በዘረጉት የጥቅም ሰንሰለት የተነሳ በሶማሊ ክልል ባለስልጣናት ላይ ምርመራ እንዳይደረግ እየተከላከሉ ነው

ጠቅላይ አቃቢ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬ በሶማሊ ክልል ውስጥ በርካታ የንግድ እና የመኖሪያ ቦታዎች ይዘው በወኪል የመሬት ሽያጭ ንግድ እንደሚያካሂዱ፣ ከእርሳቸው በተጨማሪ ዋና ዋና የሚባሉት የህወሃት ጄኔራሎች በመሬት ንግድ ውስጥ መሳተፋቸው የሶማሊ ክልል ባለስልጣናትና ወታደራዊ አዛዦች በኦሮሞ ህዝብ ላይ በፈጸሙት ወንጀል እንዳይጠቀየቁ እየተከላከሉላቸው መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል። ከክልሉ መሬት አስተዳደር ሃላፊ አቶ አብዲ ጀማል ጋር የጠበቀ ግንኙነት ያላቸው አቶ ጌታቸው፣ ሁለቱ ባለስልጣናት በክልሉ መሪ እውቅና ከፍተኛ የሆነ የመሬት ሽያጭ ንግድ እያካሄዱ ይገኛሉ። በጅጅጋ የመሬት ዋጋ ከአዲስ አበባ የመሬት ዋጋ እንደማይተናነስ የተናገሩት ምንጮች፣ በዚህም የዝርፊያ ሰንሰለት አቃቢ ህጉና የሶማሊ ክልል ባለስልጣናት ከፍተኛ ሃብትና ንብረት ሰብስበዋል። (ፎቶ አለ)

በኦሮሞ ተወላጆች ላይ ግድያና ማፈናቀል የፈጸሙ የሶማሊ ክልል ባለስልጣናት እና በክልሉ ልዩ ሃይል አዛዦች ላይ ምርመራ እንዳይካሄድ ከሚከላከሉ ባለስልጣናት መካከል አቶ ጌታቸው አምባዬ ዋናው ናቸው። የኦሮምን ህዝብ ለማረጋጋት በሚል 38 የሚሆኑ የሶማሊ ክልል ባለስልጣናትና ወታደራዊ አዛዦች እንደሚፈለጉ የፌደራል ፖሊስ ያስታውቅ እንጅ፣ እስካሁን ድረስ የተያዙት5 ሰዎች ብቻ መሆናቸውንና ከተያዙትም መካከል የተወሰኑት መለቀቃቸውን ምንጮች ተናግረዋል። አቶ ጌታቸው ትእዛዝ ካልሰጡ በክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ላይ ምንም አይነት የወንጀል ምርመራና ክስ እንደማይመሰረት የገለጹት ምንጮች፣
ከአቶ ጌታቸው አምባዬ በተጨማሪ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች በርካታ ቦታዎችን ይዘው የመሬት ሽያጭ ንግድ እያጧጧፉ ነው። እነዚህ ወታደራዊ አዛዦች በክልሉ ባለስልጣናትና የልዩ ሃይል አዛዦች ላይ ምርምራ እንዳይደረግ እየተከላከሉ ነው። እነዚህ ወታደራዊ አዛዦች በክልሉ የዘረጉት ከፍተኛ ጥቅም እንዳይቋረጥ በመስጋት ለአቶ አብዲ ሙሉ ድጋፋቸውን እየሰጡ ነው። ጄኔራሎቹ የዝርፊያ ሰንሰለቱ እንዳይታወቅባቸው ለማድረግ ደግሞ ፣ “አቶ አብዲ ከክልሉ ሃላፊነት ከተነሱ የሶማሊ ልዩ ሃይልን ይዘው ሊሸፍቱ ይችላሉ፣ አልሸባብና ኦብነግ እንደገና ተጠናክረው ሊወሩን ይችላሉ” የሚሉ ምክንያቶችን እንደሚያቀርቡ የሚገልጹት ምንጮች፣ አንዳንድ የኦህዴድ ባለስልጣናት እና የምዕራባውያን መንግስታት በሚያደርጉት ግፊት የተነሳ የሚደረገው ምርመራ የይስሙላ ሆነ እንዲቀጥል ከፍተኛ ጫና እየፈጠሩ ነው። ጄኔራሎቹ ለጊዜው በሚል አንዳንድ የሶማሊ ልዩ ሃይል አዛዦችን ከክልሉ በማውጣት እነሱ በሚቆጣጠሩዋቸው ወታደራዊ ካምፖች ውስጥ አስጠግተዋቸዋል።
የሶማሊው ክልል መሪ አቶ አብዲ ሰሞኑን ለመርማሪው ቡድን እርሳቸው የሚመሩት 13 ሺ የልዩ ሃይል ሚሊሺያ መኖሩንና በማንኛውም ጊዜ ሊጠቀሙበት እንደሚችሉ እንዲሁም ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን ከጄ/ል ሳሞራና ገብሬ ዲላ ጋር እየተመካከሩ እንደሚሰሩ ተናግረው ነበር።

No comments:

Post a Comment