Tuesday, October 6, 2015

በቴፒ ተጨማሪ ሰዎች ተገደሉ

መስከረም ፳፭ (ኅያ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከአመት በላይ ለሆነ ጊዜ በውጥረት ውስጥ የምትገኘዋ የጋምቤላና የደቡብ አዋሳኝ ከተማ ቴፒ፣ ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ ብቻ ሶስት ዜጎች ተገድለውባታል።

ከሳምንት በፊት የፌደራል ፖሊስ አባላት አንድ ሰው ከገደሉ በሁዋላ፣ ማንነታቸው በውል የማይታወቁ ሰዎች በወሰዱት የአጸፋ እርምጃ ደግሞ ከቴፒ 7 ኪሜትር እርቀት ላይ በምትገኝ ቀበሌ ውስጥ የሚኖሩ ሁለት የኢህአዴግ ካድሬዎችን ዛሬ ጠዋት ገድለዋል። ይህን ተከትሎ በአካባቢው ተጨማሪ ሃይል ተንቀሳቅሷል።

ነዋሪዎች እንደሚሉት እርምጃውን የወሰዱት ከዚህ ቀደም እስረኞችን ያስፈቱ ራሳቸውን የቴፒ ወጣቶች ብለው የሚጠሩ ወጣቶች ሳይሆኑ አይቀርም። በከተማዋ ህዝብ ይፋ ያልሆነ የሰአት እላፊ የተጣለ ሲሆን፣ ከምሽቱ 1 ሰአት በሁዋላ ሲንቀሳቀስ የተገኘ ወደ እስር ቤት ተጉዞ ድብደባ ይፈጸምበታል። ባለፉት 2 ሳምንታት ብቻ ከ10 በላይ ወጣቶች ምሽት ላይ ተይዘው ክፉኛ ተደብድበው በእስር ላይ እንደሚገኙ ነዋሪዎች ይናገራሉ።
ኢህአዴግ ብሄረሰቦችን እርስ በርስ ለማጋጨት ሙከራ ያደርጋል በማለት የሚከሱት ነዋሪዎች፣ የከተማው ህዝብ በኢህአዴግ ታጣቂዎች ላይ ጥቃት የሚፈጽሙ ወጣቶችን እንዲያጋልጥ በተደጋጋሚ ቢጠየቅም አሻፈረኝ በማለቱ፣ የፌደራሎች የበትር ዱላ አርፎበታል ይላሉ።
ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ወጣቶች አካባቢውን ለቀው ወደ አዲስ አበባ እና አጎራባች ከተሞች እየተሰደዱ ነው። ከወራት በፊት እስር ቤት ሰብረው ከገቡት መካከል ተካ የተባለው መሪ በፖሊሶች መገደሉ ይታወቃል። አንድ አባላቸውም ማእከላዊ እስር ቤት ይገኛል። ይሁን እንጅ አሁንም ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ወጣቶች ሸፍተው ለፌደራል ፖሊስ አባላት ራስ ምታት እንደሆኑ ነዋሪዎች ይገልጻሉ።
ከአመት በፊት በአካባቢው በተፈጸመ ግጭት 126 ሰዎች መገደላቸውን መንግስት አምኗል። ድርጊቱ እንዲፈጸም ትእዛዝ ሰጥተዋል ያላቸውን የዞንና የወረዳ አመራሮችን ማሰሩን ገልጿል።

No comments:

Post a Comment