Tuesday, October 6, 2015

ስልጠና ላይ ያልተገኙ የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ደሞዝ ታገደ

መስከረም ፳፭ (ኅያ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በ2008 ዓ.ም በ መንግስት ያዘጋጀውን የፖለቲካ ስልጠና ለመሳተፍ ፈቃደኛ ያልሆኑ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ደሞዛቸው እንዳይከፈል በመታገዱ የምንበላውና የቤት ኪራይ የምንከፍለው አጥተናል ሲሉ ገልጸዋል።በስብሰባው ላይ የተገኙ መምህራን ደሞዝ ሲከፈላቸው በተለያዩ ምክንያቶች ያልተሰበሰቡት መምህራን ደግሞ ደሞዝ እንደማይከፈላቸው ተነግሯቸዋል።

በአዋሳ ዩኒቨርስቲ መምህራን ወደ ውጭ እንዳይወጡ ታግደው ስልጠናውን በግድ እንዲወስዱ ተደርገዋል።

በሌላ ዜና ደግሞ ብዙ ብሄረሰቦች በሚገኙበት በደቡብ ክልል ዘረኝነት እጅግ መስፋፋቱን ወኪላችን ገልጿል፡፡ በክልሉ በሚገኙ ከተሞች የሌሎች አካባቢ ነዋሪዎች ቁጥር እየተበራከተ የሚገኝ ቢሆንም፣ የአካባቢው ተወላጆች ብቻ ስልጣን እንዲይዙና የመንግስት ስራ ላይ እነሱ ብቻ እንዲቀጠሩ መደረጉ በከተሞች ለሙስና መስፋፋትና ለስራ አጥነት ምክንያት መሆኑን የህዝብ አስተያየቶችን ሰብስቦ የላከው ሪፖርት ያመለክታል።
ፓሊሶች የአካባቢው ተወላጆች በመሆናቸው ከሌባ ጋር እየተባበሩ የከተማውን ህዝብ እንዲዘረፍና ተይዘው ሲታሰሩ ከእስር ቤት እንዲያመልጥ እንደሚያደርጉ፣ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ጉዳይ የሚፈፅሙ የመንግስት ሰራተኞች ሙስናን እንደ ዋነኛ መተዳደሪያቸው መቁጠር መጀመራቸውንም ጠቅሷል፡፡
በአንዳንድ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በተማሪዎች መካከል ከዘር ጋር በተያያዘ ፀብ እንደሚፈጠር፣ በከተሞች ተወልደው ያደጉ የሌላ ብሄር ተወላጆች ተምረው ጨርሰው ስራ አልባ እንደሚሆኑ እንዲሁም ፍትሃዊ ያልሆነ ብሄርን መሰረት ያደረገ የግብር አሰባሰብ ስርዓት እጅግ እየከፋ መምጣቱንም አክሎ ገልጿል።

No comments:

Post a Comment