Thursday, October 8, 2015

በዲመካ የተጀመረው የስራ ማቆም አድማ 3ኛ ቀኑን ያዘ

መስከረም ፳፯ (ኅያ ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደቡብ ክልል በሃመር ወረዳ በዲመካ ከተማ ማክሰኞ የተጀመረው የስራ ማቆም አድማ እስከ ዛሬ የቀጠለ ሲሆን፣ የዞኑ ባለስልጣናት ነዋሪውን ለማነጋገር ስብሰባ ጠርተዋል።

የስራ ማቆም አድማው መንስኤ ካለፉት 6 ወራት ጀምሮ በአካባቢው በመካሄድ ላይ ያለው ግጭት ስራቸውን ለመስራት ስላላስቻላቸው ነው።
የመንግስት ሰራተኞች እንደሚሉት ካለፈው ሰኔ ወር ጀምሮ በወረዳው ባሉ ቀበሌዎች ተዘዋውሮ ስራ መስራት ባለመቻሉ ፣ አብዛኛው ሰራተኛ ጊዜውን በዋና ከተማዋ ዲመካ ለማሳለፍ ተገዷል። የግጭቱ መንስኤ የልዩ ሃይል ፖሊስ አባላት አንድ የሃመር ተወላጅ መግደላቸውን ተከትሎ ቢሆንም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ፣ አርብቶአደሮቹ በአካባቢው አስተዳደሮች አንመራም፣ ከአካባቢው ተወላጆች ውጭ ያሉ ነዋሪዎች ይውጡልን የሚሉ ጥያቄዎችን አቅርበዋል።

የሰሞኑን የስራ ማቆም አድማ እንደገና የቀሰቀሰው ባለፈው ማክሰኞ ወንድምነህ እሸቴ የተባለ የኩርሜ ማዘጋጃ ሰራተኛ አስሌ በምትባል ቀበሌ ላይ በአርብቶ አደሮች መገደሉን ተከትሎ ነው። ሰራተኛው የተገደለው በሞተር ሳይክል ላይ ሆኖ ወደ ዲመካ ወረዳ ለስራ በሄደበት ወቅት ሲሆን፣ የቀብር ስነስርዓቱም በትውልድ ቦታው አርባምንጭ ከተማ ተፈጽሟል።
የሟቹን አስከሬን ለማንሳት ወደ ቀበሌው በመጓዝ ላይ የነበሩት የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ አወቀ አይቼ በአርብቶ አደሮች የመገድል ሙከራ ቢደረግባቸውም አምልጠዋል። በእርስቻው መኪና ላይ ተሰፋረው የነበሩ አንድ አዛውንት በጥይት መመታታቸውን የአይን እማኞች ገልጸዋል። ባለፈው ቅዳሜም እንዲሁ አንድ ባልና ሚስት በአርብቶአደሮች ተመተው ሆስፒታል ገብተዋል።የደህንንነት ዋስትና አጥተናል የሚሉት የመንግስት ሰራተኞች፣ በአካባቢው የሰፈረው ልዩ ሃይልም ደህንነታቸውን እንዳላስጠበቀላቸው ይናገራሉ። ከትናንት ጀምሮ ተጨማሪ ሃይል በአካባቢው እንዲሰፍር ተደርጓል።
አንዳንድ የመንግስት ሰራተኞች ለችግሩ መፈጠር ፖሊሶችንና የአካባቢውን ባለስልጣናት ተጠያቂ እያደረጉ ነው። ፖሊሶቹ የወሰዱት የተሳሳተ እርምጃና የአካባቢው ባለስልጣናት አርብቶ አደሩን እየሰበሰቡ የሚሰጡት የተዛባ መረጃ ግጭቱን ማባባሱን ሰራተኞች ይገልጻሉ።
ባለፈው ግንቦት ወር በአርብቶአደሮች እና በፌደራል ፖሊሶች መካከል በተካሄደው የተኩስ ለውውጥ 1 የመከላከያ፣ አንድ የፖሊስና 3 የልዩ ፖሊስ አባላት ተገድለዋል።
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ጉባኤ ወደ አካባቢው ሰራተኞች ልኮ በማጣራት አውጥቶት በነበረው መግለጫ፣ መንግስት በአካባቢው ለሚታየው ችግር አስቸኳይ መፍትሄ እንዲፈልግ አሳስቦ ነበር።

No comments:

Post a Comment