Tuesday, October 6, 2015

አቶ ኃ/ማርያም ደሳለኝ አዲስ ካዋቀሩት ከቢኔ 5 የቀድሞ ሚኒስትሮችን ቀነሱ

መስከረም ፳፭ (ኅያ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ጠ/ሚኒስትሩ ካላካተቱዋቸው የቀድሞ ሚኒስትሮች መካከል የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ ሶፍያን አህመድ፣ የንግድ ሚኒስትሩ ከበደ ጫኔ፣ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አለማየሁ ተገኑ፣ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አሚን አብዱልቃድር፣ የፕላን ኮምሽን ሚኒስትሩ አቶ መኮንን ማንያዘዋል ይገኙበታል፡፡

በተጨማሪም አቶ ሬድዋን ሁሴንን ከኮምኒኬሽን ሚኒስትርነት አንስተው የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስትር ያደረጉዋቸው ሲሆን፣ የህዝበ ሙስሊሙን ጥያቄ በማወሳሰብ ሲወነጀሉ የነበሩት ዶ/ር ሽፈራው ተ/ማርያም ወደ የአካባቢ፣ ደንና የአየር ንብረት ሚኒስትርነት ተዛውረዋል።

አቶ ጌታቸው ረዳ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ኃላፊ በመሆን አቶ ሬድዋንን ተክተዋል። የስልጣን ሽግሽጉ አቶ ሬድዋን ሁሴን ከወሳኝ የስልጣን ቦታዎች እየተገፉ መምጣታቸውን ያመላክታል ሲል ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍሯል።
መቶ በመቶ በኢህአዴግ አባላት የተሞላው ፓርላማ ከካቢኔ አባላት ሹመት በፊት የአስፈጳሚ አካላትን አደረጃጀት የሚቀይር ረቂቅ አዋጅ ቀርቦለት ተወያይቶ አጽድቆአል። ይህ አዋጅ ቀድሞ 23 አካባቢ የነበሩትን ሚኒስትር መ/ቤቶች ወደ 25 ያሳድጋል። በተያያዘ በግብርና ሚ/ር ስር አንድ መምሪያ የነበረው የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኮሚሽን ወደ ኤጀንሲ አድጎአል። ጠ/ሚኒስትሩ ኤጀንሲው ለድርቅ ችግር ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የተፈጥሮ አደጋዎች ይጠቅመናል ሲሉ ተደምጠዋል።

No comments:

Post a Comment