Monday, October 26, 2015

በቴፒ የመንግስት ታጣቂዎች ህዝቡን ሲያዋክቡት ሰነበቱ

ጥቅምት ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በድቡብና ጋምቤላ የድንበር ከተማ በሆነቸው ቴፒ ራሳቸውን ያደራጁ ወጣቶች በመልካም አስተዳደርና ህዝቡን አፍኖ በመግዛት ለስቃይ ዳርገውታል ባሉዋቸው የመንግስት ታጣቂዎች እና ሹማምንት ላይ የሚያደርሱትን የሃይል ጥቃት መቆጣጠር እየተሳነው የመጣው መንግስት ካለፈው አርብ ጀምሮ፣ በተለያዩ የከተማው አካባቢዎች ጥቃቱን በማስፋት ነዋሪዎች ሲያሰቃይ ሰንብቷል።

የመንግስት ታጣቂዎች፣ የነዋሪዎችን መኖሪያ ቤቶች ሰብረው በመግባት፣ ህጻን፣ አዛውንት፣ ሴት ወንድ ሳይሉ ያገኙትን የደበደቡ ሲሆን፣ አንዳንድ ወጣቶችንም ይዘው አስረዋል። ” ሽፍቶችን የሚረዳው ማን ነው፣ አውጡ?” በማለት ጥቃት ሲፈጽሙ የቆዩት ታጣቂዎች፣ የሚፈልጉትን ለማግኘት ባለመቻላቸው፣ በጅምላ ወጣቱን እያዋከቡት መሆኑን ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል።
ጥቃቱን ተከትሎ የቴፒ ወጣቶች መግለጫ አውጥተው ለኢሳት ልከዋል። መግለጫው ” የቴፒ ወጣቶች ቡድን ሰላማዊ በሆነ መንገድ ላለፉት 24 አመታት መንግስት የጫነበትን የዘረኝነት ቀንበር ለማስወገድ ሁሉም በተናጠል ሲታገል ቆይቷል” ካለ በሁዋላ፣ ሆኖም የሰላማዊ መንገድን አሻፈረኝ ያለው መንግስት ህዝቡን ሲገድል፣ ሲያስር፣ ሲፈናቅል በመቆየቱ፣ ካለፈው አመት ጀምሮ በደልና ጭቆና አንገሸገሻቸው ወጣቶች ዱር ቤቴ ብለው የህይወት መስዋትነት ለመክፈል ተገደዋል።” ሲል ያብራራል።
“የመንግስት ወታደሮች በህዝቡ ላይ እያካሄዱ ያለውን ድብደባና እንግልት እንዲያቆሙ ፣ ወታደሩ የህዝብ ልጅ መሆኑን መዘንጋት እንደሌለበትና ነገ በታሪክ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ” ወጣቶቹ በመግለጫው በማሳሰብ፣ “መንግስት በህዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ ለማስቆም ካልቻለና ለሚነሱት ጥያቄዎች መልስ መስጠት ከተሳነው፣ የመንግስት ወታደሮች የሚወስዱትን ጥቃት በመፍራት ትግላችንን አናቆምም” ብለዋል።
መግለጫቸውን ሲያሳርጉም ” ምንም እንኩዋን ጦርነትን የሚያወርስ ጦረኛ መንግስት ቢኖረንም አሁንም ቢሆን የቴፒ ወጣቶች ቡድን ሰላማዊ በሆነ መንገድ የቴፒ ህዝብ የሰላም ችግር እንዲቀረፍ ይጠይቃል፡፡ ነገር ግን ይህ ሳይሆን ቢቀር የምንከፍለዉ የህይወት መስዋእትነት በእጃችን እንደሆነ የአለም ህዝብ እንዲያቅልን እንፈልጋለን፡፡” ይላሉ።

No comments:

Post a Comment