Monday, July 30, 2018

በሃረር ወጣቶችን እርስ በርስ ለማጋጨት የተደረገው ሴራ ከሸፈ

( ኢሳት ዜና ሃምሌ 23 ቀን 2010 ዓ/ም ) ወኪላችን እንደገለጸው ጠ/ሚ አብይ አህመድን ለመደገፍ፣ በኢንጂኒየር ስመኛው ሞት ሃዘናቸውን ለመግልጽ እንዲሁም የአሟሟታቸው ሁኔታ በፍጥነት ተጣርቶ ለህዝብ ይፋ እንዲሆን ለመጠየቅና ጄ/ል አብርሃ የምስራቅ እዥ አዛዥ በነበሩበት ወቅት ታፍነው የተወሰዱትን የአቤል ፈቃዱ ወይም አቤል ኩባ እና የደረጀ ሙሉጌታ ሁኔታ ለህዝብ እንዲገለጽ ለመጠየቅ የወጡ ፋኖና ዘርማን የሚወክሉ ወጣቶችን ከቄሮዎች ጋር ለማጋጨት የተጠነሰሰው ሴራ ከሽፏል። ወጣቶቹ ጠዋት ላይ ኮከብ የሌለበትን ሰንደቃላማ ይዘው ሲወጡ፣ ለቄሮዎች “የእናንተን ትግል ለመቃወም ፋኖዎችና ዘርማዎች የተቃውሞ ሰልፍ ሊያደርጉ ነውና ተቃወሙዋቸው” የሚል መልዕክት እንዲደርሳቸው የተደረገ ሲሆን፣ የቄሮ አባላትም ወደ ወጣቶች ሄደው ከፋኖና የዘርማ አባላት ጋር ውይይት ሲያደርጉ፣ የተሰጣቸው መረጃ ሆን ተብሎ በህዝብ
መካከል ግጭት ለመፍጠር መሆኑን ሲረዱ፣ “ በሚቀጥለው ጊዜ አብረን ሰልፍ እናደርጋለን” በማለት ሴራውን አክሽፈው ተለያይተዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ሰሞኑን በቄሮ ስም የተወሰኑ ብሄሮችን እየለዩ ቤታቸውን እንዲለቁ ሲያስፈራሩ ከሹፌሮች በጉልበት ገንዘብ ሲቀበሉና ህዝቡን እያሰቃዩ ሲዘርፉ የነበሩ 6 ወጣቶች፣ በቄሮዎች ትብብር እሁድ ሃምሌ 21 ቀን 2010 ዓም ከያዙዋቸው የእጅ ቦንቦች ጋር በቁጥጥር ስር ውለዋል። በሌላ በኩል ከህወሃት አመራሮች ጋር በመሆን ለአመታት ወጣቶችን ሲያስገድልና ሲያሳፍን የነበረ አንድ ግለሰብ ማምነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ተገድሎ ተገኝቷል። በሶፊ ወረዳ ቄሌ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የተገደለው ይህ ግለሰብ፣ በአካባቢው ቄሮዎችን በማስተባበር ይመራ የነበረን ወጣት እንዲገደል ማድረጉን፣ በተለያዩ አካባቢዎች እየተዘዋወረ መንግስትን የሚቃወሙትን እየጠቆመ ሲያሳስር መቆየቱን የአካባቢው ነዋሪዎች ይገልጻሉ። ግድያውን ማን እንደፈጸመው እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም።

No comments:

Post a Comment