Tuesday, July 31, 2018

ሰመጉ በኢትዮጵያ ሶማሌ እና በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ከ700 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ገለጸ

( ኢሳት ዜና ሃምሌ 24 ቀን 2010 ዓ/ም )የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ)፣ የቀድሞው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ)፤ በኢትዮጵያ ሶማሌ እና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ዞኖች የተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በመረጃ አስደግፎ በ144ኛ ልዩ መግለጫው በዝርዝር ሪፖርቱ ከ735 ያላነሱ ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል። ከጥር 2009 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጥር 2010 ዓ.ም የተፈፀሙትን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የሚያጣሩ ባለሙያዎቹን ጥቃቱ ወደተፈፀመባቸው አካባቢዎች በመላክ የማጣራት ሥራውን ከህዳር 29 እስከ ታህሳስ 15 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ አከናውኖ፣ 258 የኦሮሞ ብሄር ተወላጆች በሶማሊ ልዩ ሃይል ሲገደሉ፣ በኦሮምያ ክልል የነበሩ 451 ሰላማዊ የሶማሊ ብሄር ተወላጆች መገደላቸውን ገልጿል። ኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ሐረርጌ ባቢሌ፣ ሐረር፣ አማሬሳ፣ ሀሮማያ፣ አወዳይ፣ ሜታ (ጨለንቆ)፣ ድሬደዋ፣ ፈዲስ፣ ኮምቦልቻ፣ ጉርሱም፣ ጃርሶ። በምዕራብ ሐረርጌ ጭሮ፣ ሚኤሶ፣ ቦርደዴ፣ መሰላ፣ ጡሎ። በምሥራቅ ጉጂ ሊበን እና ጉሚ ኤልደሎ። በምዕራብ ጉጂ ቡሌ ሆራ። በምስራቅ ሸዋ አዳማ አጣሪ ቡድኑ በመዘዋወር ምርመራዎችን አድርጓል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ጂግጂጋ
ማኔጅመንትንት፤ ኮሌጅ 1 እና ኮሌጅ 2፣ በባቢሌ፣ ሞምባስና ዱከቱ ሪፖርቱን አጠናቅሯል። በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች ከክልላችን ይውጡልን በሚል በተፈፀሙ ጥቃቶች እና ግጭቶች ምክንያት ከጳጉሜ 2009 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ታህሳስ ወር 2010 ዓ.ም. ድረስ ብቻ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በተመለከተ ባደረገው ምርመራ የበርካታ ንጹሃን ሕይወት መጥፋቱን፣ የአካል ጉዳት መድረሱን፣ ዜጎች ቤት ንብረታቸውን ጥለው መሰደዳቸውን እንዲሁም የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን ሰመጉ አረጋግጧል። በመሆኑም በተጠቀሰው ግዜ ውስጥ ብቻ ከ344 ሺህ በላይ ዜጎች ቤት ንብረታቸውን ጥለው መሰደዳቸውን በምርመራ ስራው ለማረጋገጥ ችሏል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ በሶማሌ ልዩ ኃይል በተፈፀመው ጥቃት 160 ሰላማዊ የኦሮሞ ብሄር ተውላጅ የሆኑ ዜጎች ህይወታቸውን አጥተዋል። በተመሳሳይ በባሌ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች በሶማሌ ክልል አዋሳኝ በተፈፀሙ የጅምላ ግድያዎች 98 ንፁሃን ዜጎች ተጨፍጭፈዋል። ከልዩ ኃይል በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በመከላከያ ሰራዊቱ ጥቃት 88 ሰዎች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። በዞኑ ከግድያ በተጨማሪም በሦስት ሴቶች ላይ የአስገድዶ መድፈር ወንጀልም ተፈፅሟል። አድራሻቸው የማይታወቁም መኖራቸውን ሰመጉ ዜጎችን በስም ዝርዝርና በምስል አስደግፎ አውጥቷል። በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በሚኖሩ የሶማሌ ብሄር ተወላጆች ላይ ተመሳሳይ የመብት ጥሰት ጥቃቶች መፈፀማቸውን ሰመጉ በሪፖርቱ አካቷል። ሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በተገኘ ሪፖርትና የሰመጉ ባለሙያዎች ቦታው ድረስ በመሄድ ከተጎጂዎች፣ ከተጎጂ ቤተሰቦችና ከዐይን እማኞችን በማግኘት ማጣራት አድርጓል። ይህን ዋቢ በማድረግ በኦሮሚያ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች ውስጥ በተነሱ ግጭትና ጥቃቶች ምክንያት 451 ሰላማዊ የሶማሌ ብሄር ተወላጅ ዜጎች በግፍ ተጨፍጭፈዋል። በተጨማሪም ቁጥራቸው 256 በሚሆኑት ላይ ከባድና ቀላል አካላዊ ጥቃቶች ተፈፅመውባቸዋል። ከነዚህ ውስጥ በአስር ሴቶች ላይ ኢሰብዓዊ በሆነ ሁኔታ የአስገድዶ መድፈር ወንጀሎች እንደተፈፀመባቸው ተናግረዋል። ከሰላሳ በላይ ዜጎች እስካሁን ያሉበት አድራሻ አይታወቅም። ሰመጉ በ144ኛው ልዩ መግለጫው እንዳለው በሁለቱም ክልሎች ውስጥ ለዘመናት በኖሩ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ግድያ፣ አካል ማጉደል፣ በጅምላ ማፈናቀልና የወሲብ ጥቃቶች ተፈፅመዋል። ይህን በገለልተኛ አካል በማጣራት ወንጀለኞቹን ለፍትህ አካል ማቅረብ ይገባል ሲል ሪፖርቱን አጠቃሏል።

No comments:

Post a Comment