Friday, July 20, 2018

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በአሜሪካ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚያካሂዱት ውይይት ጥላቻና መከፋፈልን በማስወገድ ለአንድ ሃገር በጋራ ለመቆም እንደሚያግዝ የጉብኝቱ የአቀባበል ኮሜቴ ገለጸ።

(ኢሳት ዲሲ–ሐምሌ 13/2010) ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በአሜሪካ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚያካሂዱት ውይይት ጥላቻና መከፋፈልን በማስወገድ ለአንድ ሃገር በጋራ ለመቆም እንደሚያግዝ የጉብኝቱ የአቀባበል ኮሜቴ ገለጸ። በዋሽንግተን ዲሲ የአቀባበል ኮሜቴ ሰብሳቢዎች በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ በሰጡት መግለጫ ላይ ይሄ ለውጥ ከመምጣቱ በፊት የችግሩ ሰለባ የሆኑ ግለሰቦች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ፊት ለፊት ለመወያየት እድሉ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሐምሌ 28/2010 በዋሽንግተን ኮንቬንሽን ሴንተር ሁሉም ኢትዮጵያዊ ያለምንም ምዝገባ ለ25 ሺ ሰዎች መድረኩ ክፍት እንደሚሆን ተገልጿል። በኋላ ላይ በሌላ አዳራሽ በሚኖረው ውይይት ደግሞ 1 ሺ 5 መቶ ሰዎች የጥያቄና መልስ እድል እንደሚሰጣቸው ተግለጿል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጡበት ጊዜ አንስቶ ኢትዮጵያውያን ያለፈውን በመርሳት አዲስ ምዕራፍ ተሰፍቶ የበኩላቸውን ለማድረግ ይሻሉ። በተለያየ ምክንያት ከሃገር የተሰደዱና በውጭ ሃገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን የለውጥ ጉዞ ይደግፋሊ። ይህ ሲባል ግን ያለፈው ግፍና በደል፣ግድያና ስቃይ እንዲረሳ
እንደማይፈልጉና ችግሩ እንዳይደገም ይሻሉ። እንዳለው በነበሩ የተባለ የአማራ ተወላጅ በኢትዮጵያ ሁለት ወንድሞቹ ከማንነት ጋር በተያያዘ በግፍ ከተገደሉበት በኋላ እሱም ከሞት አምልጦ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ መምጣቱን በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንባ እየተናነቀው ተናግሯል። የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አቀባበል ኮሚቴ ሰብሳቢ በዋሽንግተን የኢትዮጵያ አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን በወጣቱ እንዳለው በነበሩ ላይ የደረሰው ነገር እንደሰው እንደሚያሳዝናቸው ገልጸዋል። ይህ እንዳይደገምም ለውጡን በመደገፍ ሁሉም በጋራ እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል። “ግድቡን እናፈርሳለን ድልድዩን እንገነባለን”በሚል መርህ በአሜሪካ ከኢትዮጵያውያን ጋር ለመወያየት በቀጣዩ ሳምንት ዋሽንግተን ዲሲ የሚገቡት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከአሜሪካ መዲና በተጨማሪ በሎስ አንጀለስና በሚኒሶታ ከሃገራቸው ዜጎች ጋር ውይይት ያደርጋሉ። ዶክተር አብይ አህመድ በ3ቱ ከተሞች ከትውልደ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያን ጋር የሚያደርጉት ጉብኝት በሚሊየን ለሚቆጠሩ አድማጮችና ተመልካቾች በቀጥታ ስርጭት እንደሚተላለፍ ተገልጿል። በዚሁ ውይይትም ጥላቻና መከፋፈል ቆሞ ሁሉም ለሃገሩ በጋራ የበኩሉን እገዛ የሚያደርግበት ሁኔታ እንዲፈጠር ምቹ ሁኔታ ይኖራል ብለዋል።አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን። እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሐምሌ 28/2018 ቅዳሜ ቀን በዋሽንግተን ዲሲ ከ9 ኤ ኤም ጀምሮ በኮንቬንሽን ሴንተር ለ28ሺ ሰዎች አዳራሹ ክፍት ይሆናል። ዝግጅቱ ደግሞ ከ1 ፒ ኤም እስከ 4 ፒኤም ድረስ ይካሄዳል። ዶክተር አብይ አህመድ በፈረንጆቹ ሰአት አቆጣጠር ቅዳሜ ከ3 ፒ ኤም እስከ 4 ፒ ኤም ንግግር ያደጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በመለስተኛ አዳራሽ በሚካሄደው ሌላ ውይይት ደግሞ ከ1ሺ 5 መቶ የማያንሱ ሰዎች የጥያቄና መልስ ፕሮግራም ተዘጋጅቶ ምክክር እንደሚደረግ ተገልጿል። በማግስቱ እሁድ ወደ ሎስ አንጀለስ የሚያመሩት ዶክተር አብይ አህመድ በቀጣዩ ቀን ደግሞ ወደ ሚኒሶታ እንደሚያቀኑና ተመሳሳይ ውይይት ከኢትዮጵያውያን ጋር እንደሚያካሂዱ ይጠበቃል።

No comments:

Post a Comment