Monday, March 7, 2016

ኦብነግ ቻይናንና ጅቡቲን አስጠነቀቀ

የካቲት ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ግንባሩ የዓለማቀፉን የኢንርጂ ኃይል ሪፖርት ጠቅሶ ባወጣው መግለጫ – ቻይና፣ ጁቢቱና ኢትዮጵያ ተባብረው የኦጋዴንን ጋዝ ለመበዝበዝ እየሰሩ እንደሆነ በመጥቀስ፣ ከኦጋዴን -እስከ ጅቡቲ ድረስ የተፈጥሮ ጋዝን በቧንቧ ለማስተላለፍ አዲስ የሜጋ ፕሮጀክት መነደፉን እና የጂቡቲው ፕሬዚዳንትም “ዳመርጆግ” በተባለችው የጅቡቲ ከተማ የመሰረት ድንጋይ ማስቀመጣቸውን አትቷል።

ቻይና፣ ጅᎅቲና ኢትዮጵያ ይህን ውልና ስምምነት ሲያደርጉ የተፈጥሮ ጋዙ ባለቤት የሆነውን ሕዝብ ፈቃድና ሀሳብ ችላ ብለው ዘንግተው እንደሆነ ያወሳው የግንባሩ መግለጫ፤ በመሆኑም የፈለገውን ያህል መስዋእትነት ቢያስከፍልም ይህ ፕሮጀክት ከመሰራቱ በፊት የአካባቢው ህዝብ የተፈጥሮ ሀብቱንና ድንበሩን ለማስከበር ይዋጋቸዋል ብሏል።
በኦጋዴ ለሕዝብ ጥቅም የሚቆም የሕዝብ ውክልና ያለው መንግስት እስኪመሰረት ድረስ ግንባሩ በክልሉ ውስጥና ከክልሉ ውጪ የሚኖሩ የሶማሊ ተወላጆችን በማስተባበር ይህን ፕሮጀክት ለማስቆም ትግሉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብሏል-መግለጫው።
ይህ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት ከታሰበ ጀምሮ `”ፖሊ”የተሰኘው የፔትሮሊየም ኩባንያ የኢትዮጵያ ሰራዊት ወደ አካባቢው በመዝለቅ የአካባቢውን ነዋሪዎች በማፈናቀል ቦታውን እንዲያጸዱለት ክፍያ መፈጸሙን ያወሳው መግለጫው፤ በመሆኑም የኩባንያው ሰዎች የግጭቱ ምክንያትና አካል እንደሆኑ ግንባራችን ያጤነዋል ብሏል።
በፕሮጀክቱ ምርቃት ወቅት የቻይናው ፖሊ ኩባንያ ፕሬዚዳንት ሚስተር ባርቶን ዩ ፕሮጀክቱ የጅቡቲንና የኢትዮጵያን ሕዝብ ተጠቃሚ የሚያደርግ እጅግ አስፈላጊ የኢነርጅ ፕሮጀክት ነው ሲሉ ቢደመጡም፤ የኦጋዴን ሕዝብ ግን በዘዴ ከአካባቢው እንዲፈናቀል ከመደረጉ አልፎ ከፕሮጀክቱ አንዳችም ጥቅም አያገኝም ሲል የግንባሩ መግለጫ ያትታል።
የኦጋዴን አካባቢ ከሌሎች አጎራባች ሕዝቦች ጋር የሚያደርገውን የንግድም ሆነ ማናቸውንም ግንኙነት በመዝጋትና ከዓለማቀፍ ለጋሾች የሚበረከትለትን እርዳታ እንዳያገኝ በማድረግ በኩል የኢትዮጵያ መንግስት እስካሁን ድረስ ተግቶ እየተንቀሳቀሰ ነው ሲል ግንባሩ ይከሳል።
የቻይና እና የጅቡቲ መንግስታት -የኢትዮጵያ መንግስት በኦጋዴ እየፈጸመ ላለው የዘር ማጥፋት ተባባሪ መሆናቸውን ሊያውቁት ይገባል ያለው የግንባሩ መግለጫ፤ በመሆኑም እየፈጸሙት ያለው ተግባር የሚያስከትልባቸውን መዘዝ አብረው ይጋራሉ ሲል አስጠንቅቋል።

No comments:

Post a Comment