Thursday, March 24, 2016

በኢትዮጵያ ረሃቡ አስከፊ ደረጃ ላይ ደርሷል

መጋቢት ፲፭ (አሥራ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ምንም እንኳ አለማቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች ምግብና ሌሎች ተዛማች ቁሳቁሶችን መላክ ቢጀምሩም፣ የረሃቡ ሁኔታ እየከፋ መምጣቱ ታውቋል። መንግስት ከፍተኛ ችግር ያለባቸውን ቦታዎችን በደህንነት በማስጠበቅ መረጃው እንዳይወጣ ለማድረግ እየሰራ ነው። ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ የእርዳታ ሰራተኞች እንዳሉት በአፋርና በሶማሊ የሚታየው ረሃብ አስከፊ ሆነ ቀጥሎአል። በህይወቴ ቆዳቸው ከስጋቸው የተጣበቁ ህጻናትን በአይኔ አይቼ አላውቅም፣ በቅርቡ በአፋር ክልል የስደተኞች ካምፕ ያየሁት ግን መቼም ከአእምሮዬ አይጠፋም “ብሎአል። ምንም እንኳ መንግስት በሚያደርገው ቁጥጥር ምክንያት ፎቶዎችን ወይም ቪዲዮ ለማንሳት ባይቻልም፣ በድብቅ የተነሱትን መረጃዎች በቅርቡ ለኢሳት እንደሚሰጡ የእርዳታ ሰራተኛው ቃል ገብቷል።

ረሃቡ ያለበትን አስከፊ ደረጃ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም ትናንት በኔዘርላንድስ የቴሌቪዥን ጣቢያ ተላልፏል። ከአፋር አካባቢ የተቀረጸው ይህ አስደንጋጭ ፊልም ህጻናት በረሃብ የተነሳ በሞት እና በህይወት መካካል መገኘታቸውን ያመለክታል። ህጻናት አልሚ ምግብ ብቻ ሳይሆን፣ በቂ ምግብ ለማግኘት ባለመቻላቸው መጎዳታቸውን የአካባቢው የእርዳታ አስተባባሪ ዘገባውን ለሰራው ጋዜጠኛ ዮስ ቫን ዶንገን ተናግሯል። የአካባቢው ህዝብ በየ 4 ቀኑ 20 ሊትር ውሃ እየታደለው መሆኑንም ተወካዩ ተናግረዋል።
መንግስት ረሃቡ ያለበትን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ተከታታይ መረጃ ለመስጠት ባለመቻሉ፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸውን እንዳይረዱ አግዷቸዋል።
በሌላ በኩል ደግሞ ዘጋቢ ፊልሙ በኦሮምያ ክልል በመካሄድ ላይ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ በሆላንድ ኩባንያዎች ላይ ስለደረሰው ጉዳት እንዲሁም ሃይነከን የተባለው የቢራ ፋብሪካ፣ አነስተኛ ግብር በመክፈል ህዝቡን እንዴት እየበዘበዘ እንደሆነ የሚያሳይ ዘጋበ አቅርቧል። በአስተርጓሚነት ስራ የተሳተፈው የአካባቢው ተወላጅ ማንኛውም ኢንቨስተር ፣ የኦሮሞን አርሶአደር ተጠቃሚ የማያደርግ ፐሮጀክት ይዞ ከመጣ ጉዳት ይደርስበታል በማለት ተናግሯል።

No comments:

Post a Comment