Thursday, March 31, 2016

አራቱ የሚድሮክ ኢትዮጵያ ድርጅቶች ግማሽ ቢሊዮን ብር እንዲከፍሉ ተፈረደባቸው

መጋቢት ፳፪( ሃያ ሁለት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአራት የኢትዮጵያ ክልሎች የሚገኙት ባለቤትነታቸው በሚድሮክ ስር የሚገኙት ጎጀብ አግሪካልቸር፣ ሆሪዞን አዲስ ታየር፣ ሊሙ ኮፊ ፋርምና በበቃ የቡና ማቀነባበሪያ ድርጅቶች ለፕራይቬታይዜሽንና የመንግስት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ግማሽ ቢሊዮን ብር እንዲከፍሉ ሲል ፍርድ ቤቱ በይኗል።

ፍርድ ቤቱ እነዚህ አራቱ ድርጅቶች ወደ ሚድሮክ በሚዘዋወሩበት ወቅት በቅድሚያና በተወሰነ ክፍያ መክፈል የነበረባቸውን ክፍያዎች አለመፈጸማቸውን በተቀመጠላቸው የጊዜ ሰሌዳ አለመክፈላቸውን ተከትሎ ቅጣቱ መጣሉን ፍርድ ቤቱ አስታውቋል።
ሆሪዞን ፕላንቴሽን በወቅቱ ክፍያውን አለመፈጸሙን አምኖ ይህ ሊሆን የቻለው ግን በተፈጠረበት የፋይናንስ ቀውስ መሆኑንና የፋይናንስ ቀውሱ አሁንም እንዳለ ገልጿል። ድርጅቱ ካለበት የፋይናንስ ቀውስ እስኪወጣ ድረስ ተጨማሪ የስድስት ወራት የማገገሚያ ጊዜ እንዲሰጠውም ጠይቋል።
ከፍተኛው ፍርድ ቤት ስምንተኛው ችሎት ባለፈው ወር ሚድሮክ ኢትዮጵያ ያቀረበውን ክሶች ውድቅ አድርጓቸዋል። ከሚድሮክ ድርጅቶች በአጠቃላይ ለመንግስት ገቢ ማድረግ የሚጠበቅባቸው 433 ሚሊዮን 571 ሽህ 241 ብር ወደ ግማሽ ቢሊዮን አካባቢ እንዲከፈል መወሰኑን ፎርቹን ጋዜጣ ዘግቧል።
የሼህ ሙሃመድ አላሙዲን ንብረት የሆነው ሚድሮክ፣ በገንዘብ እጥረት ምክንያት ክፍያ ለመፈጸም አልቻለም መባሉ አነጋጋሪ ሆኖአል። ባለሃብቱ ትእዛዙን አክብረው ክፍያውን ይፈጽሙ አይፈጽሙ በሂደት የሚታይ ይሆናል።

No comments:

Post a Comment