Tuesday, August 18, 2015

የደቡብ ሱዳኑ ኢንፎርሜሽን ሚንስትር የስዩም መስፍንን አምባገነናዊ ሽምግልና እንደማይቀበሉት ገለፁ

ነኅሴ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሚኒስትሩ ሚካኤል ማኩዊ የምስራቅ አፍሪካ በየነ መንግስታት ኅብረት ኢጋድ ዋና አደራዳሪ የሆኑትስዩም መስፍን በተደራዳሪዎች ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድሩ ይሞክራሉ ሲሉ ወቀሳቸውን አሰምተዋል።

ሚካኤል ማኩዊ ” የኢጋድ አደራዳሪዎች ደቡብ ሱዳንን የሙከራ ምድር ለማድረግ ይሞክራሉ።አንዳንዶቹ በጭራሽ ዓለማቀፋዊ ተቀባይነት የሌላቸው ናቸው።የግድ መፈረም አለባችሁ ብሎ ለተደራዳሪዎች አስገዳጅ ውል ማቅረብ፣ ካልፈረማችሁ እኛ አንጠቀምም እንደ ማለት ሲሆን ዓለማቀፋዊ የአደራዳሪ ስነ ምግባርና ቋንቋም አይደለም።” ብለዋል።
የሰላም አደራዳሪዎቹ ማስማማት እንጂ የማስገደድና የማዘዝ ስልጣን የላቸውም የሚሉት ሚኒስትሩ፣ የኢጋድ ድርጊት ግን ፍፁም ያልተለመደና ከመደበኛ አደራዳሪዎች ያፈነገጠ ነው ብለዋል። በተለይ ዋናው የአደራዳሪዎች መሪ አምባሳደር ስዩም መስፍን ‘ወደዳችሁም ጠላችሁም ይህን ሳትፈርሙ ወደ ቤታችሁ አትሄዱም!’ ማለታቸው ግለሰቦች መንግስትን በተዘዋዋሪ ለማዘዝ መፈለጋቸውን ሲያመላክት በሌላ መልኩም አዲስ ቅኝ አገዛዝ ነው ሲሉ አክለዋል።
በሁሉም የድርድህ ሃሳቦች ዙሪያ መግባባት ላይ አለመደረሱን ሚኒስትሩ ገልጸዋል። የሰላም ስምምነቱን ተቃዋሚዎች ሲፈርሙት ፕ/ት ሳልቫ ኪር የሁለት ሳምንት እድሜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። አሜሪካ ፕሬዚዳንቱ ስምምነቱን በተባለው ጊዜ ካልፈረሙ ከፍተኛ ቅጣት ይጠብቃቸዋል ስትል አስጠንቅቃለች።

No comments:

Post a Comment